tirsdag 2. juli 2013

አቶ ስዬ በተመድ ተቀጠሩ


June 30, 2013
ከኢየሩሳሌም አርአያ
አቶ ስዬ አብርሃ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰላም አሰከባሪ ተቋም ውስጥ በወታደራዊ አማካሪነት በጥሩ ደመወዝ መቀጠራቸውን ምንጮች ጠቆሙ። በሙስና ወንጀል ተከሰው ከወንድሞቻቸው ጋር ለስድስት አመት ታስረው የተፈቱት ስዬ በተፈቱ ማግስት የአሜሪካን ድምፅ ራዲዬን ጨምሮ ለተለያዩ መገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ « ፖለቲካ ከልጅነቴ ጥርሴን የነቀልኩበትና አብዛኛው እድሜዬን ያሳለፍኩበት በመሆኑ ከትግሉ መድረክ ልርቅ ጨርሶ አልችልም» በማለት አስረግጠው መናገራቸውን እነዚሁ ወገኖች ያስታውሳሉ። «መድረክ» የሚል የፖለቲካ ስብስብ ከፈጠሩና የአንድነት አባል መሆናቸውን በይፋ ካወጁ በኋላ «ለትምህርት» በሚል ወደ አሜሪካ የመጡት ስዬ ከአንድነት ፓርቲ ሪፖርት እንዲያደርጉ የቀረበላቸውን ተደጋጋሚ ጥያቄና ማስጠንቀቂያ ችላ በማለት መልስ ለመስጠት ፈቃደኛ ሳይሆኑ መቅረታቸውን አመልክተዋል። በመጨረሻ « በቅርቡ አገር ቤት ተመልሼ ትግሌን እቀጥላለሁ » ማለታቸውን ያልሸሸጉት ምንጮቹ ስዬ ይህን በተናገሩ ሰሞን በሲያትል በተደረገ ስብሰባ ላይ « ለ21 አመት የተጀመረውን ልማትና ዲሞክራሲ እናስቀጥላለን» በማለት ብዙዎችን አንገት ያስደፋና ያሳዘነ ንግግር ማሰማታቸውን አስታውሰዋል። በአቶ መለስ ዜናዊ ሞት የተሰማቸውን ሃዘን ለመግለፅ አደባባይ መውጣታቸው ብሎም «ያሰራቸውን ስርአት ዲሞክራሲያዊ » አድርገው ለማቅረብ መሞከራቸው አስገራሚ ነበር ብለዋል።
ከሲያትሉ ስብሰባ በኋላ የኢትዮ ሚዲያ ኤዲተርን «አንተ አክራሪ ነህ» ሲሉ አቶ ስዬ ለመዝለፍ መሞከራቸውና በአንፃሩ ጋዜጠኛውም «ስዬ አንተ የተቃዋሚ ፓርቲ አትመስለኝም፤ የኢህአዴግ ባለስልጣን መሰልከኝ» በማለት እንደመለሰላቸው በስፍራው የነበሩ ታዛቢዎች ገልፀዋል። የተቃዋሚው ጎራ በተለይም «መድረክ»ን አዳክመው በመውጣት ለገዢው ፓርቲ አስተዋፅኦ አድርገዋል በማለት ብዙዎች ስዬን ይኮንናሉ። በቅርቡ ከስሚንቶ ጋር በተያያዘ በህገወጥ ንግድ ተሰማርተው ተገኝተዋል የተባሉትና የ«ምፍአም ትሬዲንግ» ባለቤት የሆኑት የስዬ ወንድም ምህረትአብ አብርሃ በድጋሚ በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው የታሰሩ ሲሆን፣ ከዚህ ቀደም በሙስና ወንጀል ተፈርዶባቸው የእስር ጊዜያቸውን ጨርሰው እንደወጡ ይታወቃል። ከዚሁ ክስ ጋር በተያያዘ አቶ ስዬን ጨምሮ የሁሉም ወንድሞቻቸው የባንክ አካውንት እንዲታገድ ተደርጓል። « ስዬ የባንክ አካውንት እንኳ የለኝም » ሲሉ እንደቆዩ ያስታወሱት ምንጮች « አሁንስ ስዬ ምን ይሉ ይሆን?…ምን ያክል ገንዘብ በባንክ አስቀምጠው ይሆን?» በማለት ይጠይቃሉ።

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar