mandag 30. juni 2014

አንጋፋው የነጻነት ታጋይ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ በየመን የፀጥታ ሃይሎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ግንቦት 7 ዛሬ አስታውቋል::

June 30, 2014
ግንቦት 7 ዛሬ ለጋዜጠኞች እና ለአባላቶቹ በላከው መግለጫ የድርጅቱ ዋና ጸሃፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ለስራ በሚንቀሳቀሱበት ሰአት ትራንዚት በአደረጉበት በየመን አውሮፕላን ጣቢያ ውስጥ በፀጥታ ሃይሎች መወሰዳቸውን አስታውቋል።
ginbot 7
ንቅናቄው የየመን መንግስት አቶ አንዳርጋቸውን ለወያኔ አሳልፎ እንዳይሰጥ ከፍተኛ የሆነ ማስጠንቀቂያ የላከ ሲሆን ለሳምንት ያህል ውስጥ ለውስጥ ሲደረግ የነበረው ውይይትም በሁለቱ ወገኖች ሳይሳካ መቅረቱን በመግለጽ የመን ይህን ታሪካዊ ስህተት ብትፈጽም በወደፊቱ የሁለተዮሽ ሀገራት ግንኙነት ላይ የማይጠፋ ጠባሳ እና አስቸጋሪ ሁኔታ እንደሚፈጠር አስታውቋል፡፡
ድርጅታችን የሚያደርገውን የነጻነትና የዲሞክራሲ ትግል ከቶ ለአንዳፍታም ቢሆን አያቆምም ያለው ድርጅቱ፤ አቶ አንዳርጋቸው ራሳቸውን አሳልፈው ለሚወዷት ሀገራቸው እማማ ኢትዮጵያ መሰዋእት ለመሆን የተዘጋጁ የኢትዮጵያ የቁርጥ ልጅ መሆናቸውን እና መላው የኢትዮጵያ ህዝብ በዚህ አስቸጋሪ ሁኔታ ከጎናችን ሆኖ ትግሉን እንዲያጠናክርና  በየመን መንግስት ላይ ህዝቡ በያለበት ጫና እንዲያደርግ ጥሪ አቅርቧል።
እንደሚታወቀው በአለፉት ወራቶች የኢትዮጵያ መንግስት በአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ላይ የመግደል ሙከራ ማድረጉ የሚታወስ ነው።
ሙሉ መግለጫውን በሚቀጥለው  እናወጣለን።
በዚህ አጋጣሚ አባይ ሚዲያ በየመን መንግስት ያደረበትን ከፍተኛ ቅሬታ እየገለጸ ሁሉም የኢትዮጵያ ልጆች ለዚህ አንጋፋ የነጻነት ታጋይ አንዳርጋቸው ጽጌ ተላልፎ እንዳይሰጥ በውጭ የምትኖሩ ኢትዮጵያውያን በሙሉ በየመን እና በአለም አቀፍ የተባበሩት ቢሮዎች የተቃውሞ ድምጻችን እንድናሰማ ጥሪያችን እናቀርባለን፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ የሚደርሱንን ማናቸውም መልእክትና ጽሁፍ ቅድሚያ በመስጠት ድህረገጻችን ላይ እንለጥፋለን።

søndag 29. juni 2014

The staged ‘hearing’ of the three bloggers Abel, Befeqadu and Mahlet concluded with another appointment for 6th time

zone 9
A Brief hearing yet very late start
The dramatic Sunday morning hearing was adjourned before it even started a the court registrar did not show up for the hearing but yet again set to continue as the registrar popped up out of nowhere. The judge decided to proceed with hearing that did not last for more than ten minutes and the hearing is adjourned for Monday 14th of July 2014 even though the police asked for more additional two weeks. The hearing started at least thirty minutes later than its scheduled time.
Police Harassment
More than 300 hundred people have appeared to Arada First Instance Court to show solidarity with bloggers among which two individuals who tried to take a picture of the bloggers while they are being escorted to the court room are detained by the police. The fate of the detained individuals is not instantly clear. However eye witnesses detailed through their Twitter that individuals were harassed by the police. Attendees reported that the security was intense and the police forced them out from court ground.
False Confessions & Frustrations
Befeqadu Hailu reported to the court that he is made to make false confessions. He told the court anything which will come against him is not his confessions. The people who are forced to attend the hearing from a distance are frustrated and they compare the situation with an occupied militarily zone. The attendees waved their hands in greetings and give a message of support while the bloggers being escorted to the court room but police denied the crowd not to greet them by making the bloggers stay in the court room until crowd dispersed.
Soruce: Zone9ers ‘Trial’
Ze-Habesha Website may contain advice, opinions, and statements of various information and content providers. The Website neither represents nor endorses the accuracy of information or endorses the contents provided by external sources. All blog posts and comments are the opinion of the authors.

[የዞን 9 ጦማርያን የፍርድ ቤት ውሎ] ልም››


በዛሬው "የፍርድ ቤት" ውሎ ፓሊስ 28 ቀናት የተጨማሪ ምርመራ ጊዜ ጠይቆ 15 ቀናት ተፈቅዶለታል

ዛሬ በአራዳ አንደኛ ደረጃ "ፍርድ ቤት" አንደኛ ምድብ ወንጀል ችሎት ሶስቱ የዞን 9 ጦማሪ ጓደኞቻችን የቀረቡ ሲሆን ፓሊስ ለ28 ቀናት ተጨማሪ ጊዜ ቀጠሮ ሲጠይቅ "ፍርድ ቤቱ" 15 ቀናትን ሰጥቶታል፡፡ በእለቱ የነበሩት ዳኛ ይህ ጉዳይ በጣም ተራዝሟል በሚል 15 ቀን መፍቀዳቸው የተሰማ ሲሆን ችሎቱ የተሰየመው ለ10 ደቂቃ ላነሰ ጊዜ ነበር፡፡ ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ እስር ቤት ውስጥ እሱ ያላለውን ቃል በመጻፍ እንዲያምን በፓሊስ መገደዱንና የሱ ቃል እነዳልሆነ ለ"ፍርድ ቤቱ" የተናገረ ሲሆን ዳኛዋ ይህ ችሎት ያንን የማይመለከት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

"የፍርድ ቤቱ" ቅጥር ግቢ ውስት ከ300 በላይ የሚጠጉ የጦማርያኑ ጓደኞች እና ቤተሰቦች የተገኙ ሲሆን በተለይ ይህ ሁለተኛ ቡድን "ፍርድ ቤት" በሚቀርብበት ወቅት የሚታየው በፓሊሶችና ለታሳሪዎቹ አጋርነት ለማሳየት በመጡ ወዳጆች መካከል ከፍተኛ ውጥረት ዛሬም ታይቷል፡፡

ፓሊስ ፎቶ ለማንሳት ሙከራ ያደረጉ ሁለት ወጣቶችን እና የነሱን መያዝ ላይ ጥያቄ የጠየቀ አንድ ወጣትን በጥቅሉ ሶስት ሰዎችን በቁጥጥር ስር ማዋሉ ታውቋል፡፡(ሁለቱ ወጣቶች የሰማያዊ ፓርቲ አባላት መሆናቸውም ተረጋግጧል) ችሎቱ ከተጠናቀቀ በኋላ ወዳጆቻቸውን ሲወጡ ለመመልከት በፍርድ ቤቱ ጊቢ ይጠበቁ የነበሩ ሰዎችን ፓሊስ ከግቢው አስገድዶ ለማስወጣት ባደረገው ጥረት ውጥረት ሰፍኖ የነበረ ሲሆን ለመጻፍ የሚከብዱ አጸያፌ ስድቦችን ፓሊሶች ሲሳደቡ እነደነበረ በቦታው የነበሩ ወዳጆች ሪፓርት አድርገዋል፡፡ በስተመጨረሻም ታሳሪዎቹ ቅጥር ጊቢውን ለቀው ሲወጡ ለማየት ያልተፈቀደ ሲሆን የ"ፍርድ ቤቱ" በር ተዘግቶባቸው መንገድ ላይ ሲጠብቁ የነበሩም ወዳጆቻቸው የማየት እድሉ ሳይገጥማቸው ተመልሰዋል፡፡ ፓሊስም አድማ በታኝ እንጠራለን የሚል ተደጋጋሚ ማስፈራሪያ ሲያሰማ ነበር፡፡

ከፍተኛ የፓሊስ ስርአት አልባነት የተንጸባረቀበት ይህ ሂደት የፍትህ ስርአቱ መገለጫ ሲሆን የዞን ዘጠኝ ጦማሪ ጓደኞቻችን በምንም አይነት ህገ ወጥ ተግባር ላይ ተሰማርተው አንዳልነበረና ክሱም ሃሳባቸውን በነጻነት በመግለጻቸው የተመሰረተ ፓለቲካዊ ክስ መሆኑን ለማስታወስ አንወዳለን፡፡

ፍርድ ቤት ለተገኛችሁ ሂደቱን በተለያዩ መንገዶች ሪፓርት ስታደርጉ ለነበራችሁ እና አጋርነታችሁን ላሳያችሁ ዞን 9 ነዋሪያን በታሰሩ ወዳጆቻችን ስም ከፍ ያለ ምስጋናችንን እናቀርባለን

ኢትዮጵያዊው-ኖርዌጂያን ኦኬሎ ኦካይ ኦቻላ ”ሞት ሊበየንበት ይችላል” -በሽብርተኝነት ክስ ሞት ተፈርዶባቸው ሞታቸውን የሚጠባበቁ 127 ሰዎች ኣሉ

በኖርዌይ ሃገር ውስጥ በኖርዌጂያንኛ የሚታተመው ዳግብላደት የተባለው ጋዜጣና ድረ-ገጽ ”ኢትዮጵያዊው-ኖርዌጂያን” ኦኬሎ ኦካይ ኦቻላ በሚቀጥለው ሳምንት ሞት ሊበየንበት ይችላል” ሲል ኣውጥቶኣል።
”ባለፈው ሳምንት ለማወቅ እንደተቻለው ዕድሜው 52  የሆነና  ኦኬሎ ኦካይ ኦቻ  የተባለ ኖርዌጂያን ኢትዮጵያ ውስጥ በሽብርተኝነት ተከሶ በእስር ላይ ይገኛል።” tiltalt for terror በማለት የጀመረው የኖርዌዩ ዳግብላደት ሲቀጥልም…”የኢትዮጵያ መንግስት ቃለ ኣቀባይ እንደሚለው ገንዘብ ኣሰባስቦና ኣጥቂ ቡድን መልምሎ ኣደጋ ለማድረስ ሲሞክር ያዝነው በማለት መከሰሱን ያትትና በበኩላቸው የኖርዌዩ የሰብኣዊ መብት ጥበቃም ሆኑ የዓለም ኣቀፉ ሰብኣዊ መብት ተሟጋቾች ድርጊቱን በጥብቅ ያወገዙት ሲሆን፣ ኣያይዘውም ለዚሁ ድረ-ገጽ ታሳሪው ግለሰብ ያለበት ሁኔታ ከወትሮው የከፋ እንደሆነም ስጋታቸውን እንደገለጹለት ያወሳል።
 ኢትዮጵያንም ሆነ የቀድሞው የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት፣ በኣሁኑ ወቅት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ውስጥ የሚገኙትን  ኦኬሎ ኦካይ ኦቻ ”በሚገባ ያውቃሉ” ያሉዋቸውን የሰብኣዊ መብት ተሟጋችና ኖርዌጂያን ፈሊክስ ሆርነ ን  ኣነጋግሮ ድረ-ገጹ ያገኘው መልስ ”ኖርዌጂያኑን ኦኬሎ በሚቀጥለው ሳምንት የሚሰየመው ችሎት ሞት ሊበይንበት ይችላል” በማለት የገለጹ ሲሆን ኣክለውም፣
”በሃገሪቷ ውስጥ በሽብር ወንጀል የሚከሰሱት ዜጎች የሚገጥማቸው የሞት ፍርድ ነው። ነገር ግን እነዚህ ሞት የሚፈረድባቸው ዜጎች ምንም ማስረጃ ያልቀረበባቸው ናቸው። በሽብር ክስ ስለተከሰሱ ብቻ ዕድላቸው ይሄው ነው። በሞት ቀጠና የሚገኙትን ዜጎች የሚዘግበው ዓለም ኣቀፉ ድርጅት በኢትዮጵያ በእስር ቤት ውስጥ በሞት ቀጠና (ሴል) የሚሰቀሉበትን ወይም የሚገደሉበትን ጊዜ የሚጠባበቁ 127  ዜጎች  ይገኛሉ ሲል ፈሊክስ ሆርነ ለድረ- ገጹ ገልጸዋል።
 ሌላው ኣምነስቲ ኢንተርናሽናል ውስጥ የሚሰሩት ጌራልድ ካዶርድ ”የኢትዮጵያ መንግስት ኦኬሎን እንደከሰሰው በሽብር ወንጀል ጦር ሲመለምልና ሲያደራጅ ኣግኝቶት ከሆነ፣ የሞት ቅጣት ይበይኑበታል የሚለው ስጋቴ ነው።የፍርድ ሂደቱን እንደምናየው የሞት ቅጣቱ በፍርድ ቤቱ ይለወጣል የሚል ዋስትና የለንም።” ኣያይዘውም ባለፈው ዓመት 8 ጋምቤላ ውስጥ ያሉ የተቃዋሚ ድርጅት ኣባላቶች በሽብርተኝነት ከሰዋቸውና የሞት ፍርድ በይነውባቸው ሞታቸውን በመጠባበቅ ላይ ናቸው።”
 ጭፍጨፋ
ኦቻላ ከሽብርተኛ ጋር ግንኙነት እንዳለው ኣላውቅም። ነገር ግን በጋምቤላ ውስጥ መንግስትን የሚቃወም ጠንካራ ተቃዋሚ ድርጅት የለም። መንግስትን ለመቃወም የሚነሱትንም ሽብርተኛ የሚል ስም በክልሉ መንግስት ይለጠፍባቸዋል።
 ኦቻላ የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት የነበረ ጊዜ፣ massakre 13. desember 2003. የ 1000 በላይ  የኣባወራዎች መኖሪያ ቤቶች በገዥው ስርዓት ወታደሮች ሲቃጠልና ከ400 የኣኙዋክ ንጹሃን ተወላጆች በጥይትና በስለት ሲታረዱ በስፍራው  ነበር። ይሄንንም ተከትሎ ወደ ደቡብ ሱዳን ስልጣኑን በመተው መሰደዱንና ከዚያም ከቤተሰቡ ጋር  በኖርዌይ ”ትሮንዳሄም” በተባለ ቦታ  በስደተኝነት በመግባትና ፈቃድ ጠይቆ በ2009 ዓ.ም የኖርዌጂያን ዜግነት ተሰጥቶት ነበር።
  ቢሆንም  ከ 2012 ጀምሮ በጋምቤላ ውስጥ በሚከናወነው ሁኔታዎች ይረበሽ ነበር። በዚህም የተነሳ ወደዚያው ኣቅንቶኣል።ማድረግ ግን ኣልነበረበትም።በኣንድ ወቅት በክረምት ወራት የሱዳን የመረጃና ደህንነት ሰራተኞች በሱዳን ጁባ ውስጥ ያለን ኣንድ ሆቴል በድንገት ከበቡት። ከዚያም በውስጡ የነበሩትን የሱን ጓደኞች  ኣስረዋቸው ወደ ኢትዮጵያ  ልከዋቸዋል በማለት ድረ- ገጹ ኣትቶኣል።
ቶርቸር 
በኣሁኑ ሰዓት ኦኬሎ በእስር ቤት ውስጥ ባልተረጋገጠ መረጃ ውስጥ ይገኛል። ይህ ኖርዌጂያን በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ማወቅ ኣይቻልም።በኢትዮጵያ ውስጥ በሽብርተኝነት በእስር ቤት ውስጥ ሆኖ  የእናትነት እንክብካቤን ማግኘት ህልም ነው።እስረኞች ለቶርቸርና ስቃይ የተጋለጡ  መሆናቸውን ፈሊክስ ሆርነ  ለድረ-ገጹ ኣስረድተዋል።
የኦኬሎን የፍርድ ሁኔታ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኘው ሪፖርተር የተሰኘው  ጋዜጣ ችሎቱ  ጁላይ 1 ይውላል ብሎ ቢገልጽም፣ የእኛ Dagbaldet በሲዊድን ያለውን የኢትዮጵያ ኣምባሳደር ለማግኘት ሞክረን ያልተሳካልን ሲሆን፤ ዓለም ኣቀፉን የሰብ ኣዊ መብት ተሟጋች ድርጅትንም ሆነ በኣዲስ ኣበባ ካለውም የኖርዌይ ኤምባሲ ትክክለኛ የችሎት ጊዜውን ማረጋገጥ ኣልተቻለም።
የኖርዌይ የውጭ ጉዳይም ለኣንድ ኣዲስ ኖርዌጂያን በኣደጋ ውስጥ በሚሆንበት ጊዜ፣ ወይም ኣደጋ በገጠመው ወቅት እንዴት መከላከል  እንዳለበት ከድረ- ገጹ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ መስጠት ኣልፈለጉም።ድረ- ገጹ   ምላሽ በማጣቱም ይመስላል በኮንጎ ውስጥ ኖርዌጂያዊው Joshua French  በሞት ሲቀጣና፣  Shahid Azim  በኣስገድዶ መድፈር ወንጀል ፖኪስታን ውስጥ ተይዞ ሞት ሲፈረድበትም ኣላስጣሉትም በሚል ኣጣቅሰው ያለፉት። ቢሆንም ይላሉ የውጭ ጉዳይ ቃል ኣቀባይ ፍሮደ ኣንደርሰን፥ እስከኣሁን ከተከሳሹ ስለ ፍርድ ውሳኔውንም  ሆነ  ስለ ችሎቱ ቀን የምናውቀው የለም በማለት ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ ያለው የኖርዌይ ኣምባሳደር  ኦኬሎ ኦካይ ኦቻላን በተመለከተ ተደጋጋሚ  ጥያቄዎችን ለኢትዮጵያ መንግስት ኣቅርቦኣል። ኦኬሎ ያለበትን ሁኔታ፣ የፍርድ ሂደቱን ለመከታተልና በእስር ቤት ለመጎብኘት፣ ቢሆንም  ከኢትዮጵያ መንግስት ምንም  ምላሽ  ኣልተገኘም። የኖርዌይ የውጭ ጉዳይ ቢሮ ሁኔታውን በኣደገኛነት እንደሚያዩትም ሳይገልጹ ኣላለፉም።
ባለፈው ሳምንት  የኦኬሎ ባለቤት ኦባ ኦድዋ ኦመት kona Obo Adwo Omot fram i Dagbladet  ”… ባለቤቴ ሽብርተኛ ሳይሆን የፖለቲካ እስረኛ ነው” በማለት ገልጻ ነበር። ይህችው የ ኣራት ልጆች እናት የሆነችው ባለቤቱ ባለፈው ሳምንት እንደገለጸችው፣ ”…በኣሁኑ ሰዓት በዚህ ጠባብ ክፍል ከኣራት ልጆቼ ጋር እገኛለሁ። ምንም የማውቀው ነገር የለም። ባለቤቴም የሚያውቀው ነገር የለም። የኖርዌይ መንግስት የተቻለውን ሁሉ ኣድርጎ ባለቤቴን ከእስር እንዲያስወጡልኝ እማጸናለሁ በማለት ነበር የገለጸችው።

እያበበ የመጣዉ ህዝባዊ ትግል

ኢትዮጵያ ህዝብ ለብዙ ዘመናት እንወድሀለን በሚሉት ነገስታት ተረግጧል፤ ህብረተሰብዓዊነት አመጣንልህ ባሉት ወታደራዊ አምባገነኖችም ለ17 አመት እጅና እግሩን ታስሮ ተገዝቷል። እነዚህ ሁለት ለህዝብ ደንታ የሌላቸዉ መንግስታት ተራ በተራ በህዝብ ትግል ተንኮታኩተዉ የታሪክ ቅርጫት ዉስጥ ገብተዋል፤ ሆኖም ሁለቱንም መንግስታት በመራራ ትግል አሸንፎ የጣለዉ የኢትዮጵያ ህዝብ የትግሉን ዉጤት ማስጠበቅ ባለመቻሉ ይህ ኃያልና የረጂም ዘመን ታሪክ ባለቤት የሆነ ህዝብ ዛሬም ነፃ አወጣንህ በሚሉት ዘረኛ አምባገነኖች እየተረገጠ ነዉ። አዎ! የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬም እየተረገጠ ነዉ። ዛሬም አየታሰረ ነዉ። ዛሬም እየተገደለ ነዉ። ዛሬም ይህንን ሁሉ በደል የሚያደርሱበትን የአንድ ወንዝና የአንድ መንደር ምርት የሆኑ ዘረኛ አምባገነን ገዢዎችን ከጭንቅላቱ ላይ ለማዉረድ እየታገለ ነዉ። በእርግጥም የኢትዮጵያ ህዝብ ከምን ግዜም በተለየ መልኩ የወያኔን ዘረኛ አገዛዝ አምርሮ እየታገለ ነዉ፤ በተለይ በዚህ በያዝነዉ አመት ወያኔንና ሃያ ሁለት አመት ሙሉ የገነባዉን ዘረኛ ስርዐቱን ለመደምሰስና ኢትዮጵያ ዉስጥ በፍትህና በእኩልነት ላይ የተመሰረተ ስርዐት ለመገንባት የሚደረገዉ የሞት የሽረት ትግል ተጠናክሮ ቀጥሏል።
ወያኔ እግሩ አዲስ አበባን ከረገጠበት ግዜ ጀምሮ የጭቆና ተቋሞቹን በየቦታዉ ተክሎና ተደላድሎ ህዝብን እንዳሰኘዉ መርገጥ እስከጀመረበት ግዜ ድረስ አንዴ ሰዉ በላዉን የደርግ ስርዐት አስወገድኩላችሁ እያለ ሌላ ግዜ ደግሞ ፌዴራል ስርዐት መስርቼ ብሄር ብሄረሰቦችን ነፃ አወጣሁ እያለ ለተወስነ ግዜም ቢሆን የኢትዮጵያን ህዝብ ቀልብ መሳብ ችሎ ነበር። ሆኖም ብዙም ሳይቆይ ያ በፌዴራሊዝም፤ በዲሞክራሲና በይስሙላ ምርጫ የተሸፈነዉ የወያኔ አስቀያሚ ገበና ይፋ እየሆነ መጥቶ ወያኔ አርግጫዉንና ግድያዉን የኢትዮጵያ ህዝብ ደግሞ ትግሉን፤ እስሩንና ስደቱን ተያያዙት።
የወያኔን መሰሪ አላማ ገና ከጧቱ የተረዱ ኢትዮጵያዉያን ባለፉት ሃያ ሦስት አመታት ይህንን መሰሪ አገዛዝ በተደራጀ፤ ባልተደራጀ፤ በተባበረና በተበታተነ መልኩ ሲታገሉ ቆይተዋል። ሆኖም የአገራችንን የፖለቲካና የኤኮኖሚ መዋቅሮች ሙሉ ለሙሉ ከሚቆጣጠረዉ ወያኔ ጋር በቁጥር፤ በአይነትና በይዘት የሚመጥን ትግል ማካሄድ ባለመቻላቸዉና እንዲሁም ብትራቸዉን ወያኔ ላይ ብቻ ከመሰንዘር ይልቅ እርስ በርስ ስለሚላተሙበት ምንም አይነት ህዝባዊ ድጋፍ በሌለዉ ወያኔ ላይ የትግል የበላይነት ማግኘት አልቻሉም፡፡ ወያኔም እኛዉ ዉስጥ ከመካከላችን የበቀለ እሾክ በመሆኑና ደካማ ጎናችንን በሚገባ ስለሚያዉቀዉ በዚሁ ደካማ ጎናችን እየገባና እርስ በርስ እያባላን የስልጣን ዘመኑን እስከዛሬ ማራዘም ችሏል።
ወያኔ የአንድን አካባቢ ህዝብ ከሌላዉ አካባቢ ህዝብ፤ አንዱን የህብረተሰብ ክፍል ከሌላ የህብረተሰብ ክፍል ጋር በሆነዉ ባልሆነዉ ምክንያት እየፈጠረ ማጋጨቱን አሁንም አላቆመም፤ እንዲያዉም ይበልላችሁ ብሎ በስፋት እንደቀጠለበት ነዉ። ዘንድሮ ግን ህዝብ፤ የተቃዋሚ ኃይሎችና በወያኔ ተንኮል ተታልለዉ የእርስ በርስ ሽኩቻ ዉስጥ ገብተዉ የነበሩ የህዝብ ወገኖች ሁሉ የወያኔን የከፋፍለህ ግዛዉ ደባና ሴራ በሚገባ ያወቁ ይመስላል። ለምሳሌ በቅርቡ አምቦና በተለያዩ የኦሮሚያ ክልል ዩኒቨርሲቲዎች ዉስጥ ከፍተኛ ፀረ ወያኔ የተቃዉሞ ሰልፍ በተካሄደ ግዜ የወያኔ ካድሬዎች የኦሮሞ ህዝብ ቁጣና መነሳሳት አቅጣጫዉን ቀይሮ በትግል አጋሩ በአማራ ህዝብ ላይ እንዲያተኩር ለማድረግ ያልፈነቀሉት ዲንጋይ አልነበረም። ሆኖም ወያኔን ከስልጣን ለማባረርና የአገራቸንን ወደፊት በህዝብ እጅ ላይ ለማስቀመጥ ቁልፉ መተባባርና አንድ ላይ መቆም መሆኑን የተረዳዉ የኦሮሞና የአማራ ህዝብ ቁጣ ይበልጥ በወያኔ ላይ ነደደ እንጂ አንደቀድሞዉ ለወያኔ የተንኮል ሴራ እጁን አልሰጠም።
ወየኔን በተለያዩ የትግል ስልቶች የሚፋለሙ የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ኃይሎች በፀረ ወያኔ አቋማቸዉና በአላማቸዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ሙሉ ድጋፍ ከጎናቸዉ እንዳለ እንኳን እኛ ወያኔም በሚገባ ያዉቃል። ህዝብን የመሰለ እንደ ዉኃ ማጥለቅለቅ የሚችል ኃይል ከጎናቸዉ ያሰለፉ ድርጅቶች ደግሞ ወያኔን የመሰለ ምንም ህዝባዊ መሰረት የሌለዉን ኃይል ቀርቶ ፊታቸዉ ላይ የቆመን ምንም አይነት ኃይል ከማሸነፍ የሚገታቸዉ ምንም ነገር የለም።
ሆኖም ዉኃም ቢሆን ምን ያክል ኃይለኛ መሆኑ የሚታወቀዉ ተገድቦ ወደ ተፈለገበት አቅጣጫ እንዲሄድ ሲደረግ ነዉና የኢትዮጵያ ተቃዋሚ ኃይሎችም ከጎናቸዉ የቆመዉን ህዝብ አስተባብረዉ አገራችንን ወደ ድል መምራት የሚችሉት መጀመሪያ እነሱ ተባብረዉ ህዝብን በአንድ አላማና በአንድ አመራር ስር ማሰለፍ ሲችሉ ብቻ ነዉ። ዛሬ በሁሉም አካባቢዎች ባይሆንም አገር ዉስጥና ካገር ዉጭ በተለያዩ አካባቢዎቸ ይቅናችሁ በሚያሰኝ መልኩ ጎልተዉ የሚታዩ ብዙ የትብብርና የትግል ቅንጅት ጅምሮች አሉ። በገበሬዉና በሰራተኛዉ፤በወጣቱና በወታደሩ በተለይ ደግሞ በተለያዩ ብሄረሰቦችና በተለያዪ የፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ከመለያየት ይልቅ የመቀራረብ፤ ከመወቃቀስ ይልቅ የመወያየት ከመጠላለፍ ይልቅ የመተቃቀፍ አዝማሚያዎች በብዛት እየታዩ ነዉ።
ከ1997ቱ ምርጫ በኋላ ጀምሮ እስከቅርብ ግዜ ድረስ የተቃዋሚዉን ጎራ በተለይም አገር ዉስጥና ከአገር ዉጭ የሚገኙትን የኢትዮጵያ የፖለቲካ ልህቃን ለሁለት ከፍሎ ሲያጨቃጭቅ የከረመዉ ወያኔን በህዝባዊ አመጽ ወይስ በህዝባዊ እምቢተኝነት ታግለን እናዉርደዉ የሚለዉ ጥያቄ ዛሬም ድረስ አዎንታዊ እልባት ባያገኝም ዛሬ ሌላ ቢቀር እንደቀድሞዉ የተቃዋሚዉን ጎራ ለሁለት ከፍሎ የወያኔ መጠቀሚያ ማድረግ አይችልም። የኢትዮጵያ ህዝብም እኔ ያለሁት ጉድጓድ ዉስጥ ነዉና ወይ ተደጋግፋችሁ አዉጡኝ አለዚያም በቻላችሁትና በሚታያችሁ መንገድ አዉጡኝ ነዉ የሚለን እንጂ በኛ መጨቃጨቅ የሱ የጉድጓድ ዉስጥ ቆይታ ዬትየለሌ እንዲሆን አይፈልግም። ዛሬ ይህንን ተደጋግፋችሁ ነጻ አዉጡኝ የሚለዉን የኢትዮጵያ ህዝብ ጥሪ ሰምተዉ በየጫካዉና በየበረሃዉ ከወያኔ ጋር የሞት የሽረት ትግል ለማድረግ የቆረጡ ኃይሎች የሚያደርጉት መሰባሰብና በተባበር ወገንን እጅግ የሚያበረታታ ጠላትን ደግሞ ያንኑ ያክል የሚያንቀጠቅጥ መልካም ጅምር ነዉ።
ከተለያዩ የአገራችን ኣካባቢዎችና ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተዉጣጥተዉ ወያኔን በሚገባዉ ብቸኛ ቋንቋ ለማነጋገር ቆርጠዉ የተነሱት የኢትዮጵያ ልጆች ወያኔን አንከባልለዉ የሚጥሉት ባነገቡት ጠመንጃ ብቻ ሳይሆን በህብረታቸዉና በአላማ ጽናታቸዉ እንደሆነ በሚገባ ያዉቃሉ። ለዚህም ነዉ ዛሬ እነዚህ ጀግኖች ባሉበት ጫካና በረሃ ሁሉ የሚሰማዉ መዝሙር . . . . ላንቺ ነዉ ኢትዮጵያ . . . ላንቺ ነዉ… ላንቺ ነዉ ኢትዮጵያ ላንቺ ነዉ… ላንቺ ነዉ ኢትዮጵያ ደሜን የማፈሰዉ የሆነዉ።
ዛሬ አገራችን ኢትዮጵያን ከዘረኞችና እነሱ ከገነቡት ዘረኛ ስርዐት ለማላቀቅ ዉስብስብነት ገብቷቸዉ ይህንን ዉስብስብ ትግል ከመታግል ዉጭ ሌላ ምንም አማራጭ እንደሌለ ተረድተዉ የትግል ህብረትና አንድነት የጀመሩ ብዙ ወገኖች አሉ። ይህ የሚያበረታታና ተስፋዉ የለመለመ ጅምር የሁላችንም ድጋፍና ተሳትፎ የሚያስፈልገዉና አለንልህ ሊባል የሚገባዉ አገራዊ ጅምር ነዉ። በዚህ ጅምር ዉስጥ ትንቅንቅ አለ፤ በዚህ ጅምር ዉስጥ መስዋዕትነት አለ፤ በዚህ ጅምር ዉስጥ ድል አለ። በህዝባዊ እምቢተኝነቱ ጎራ ከቅርብ ግዜ ወዲህ በብዙ የኢትዮጵያ ከተማዎች ዉስጥ ህዝቡ የወያኔን ግልምጫ፤ እስርና ድብደባና ግድያ ከምንም ባለመቁጠር በየአደባባዩ ወያኔን ፊት ለፊት መጋፈት ጀምሯል። ወያኔን በብዕራቸዉ የሚታገሉ ወጣቶችም ከዘላለም ባርነት የአንድ ቀን ነጻነት ይሻለናል ብለዉ በሰላ ብዕራቸዉ ህዝብን እንዳስተማሩ ቃሊቲ ወርደዋል። በህዝባዊ አመጹ ጎራ ደግሞ የአባቶቹን ታሪክ ለመድገም ቆርጦ የተነሳዉ የኢትዮጵያ ወጣት አዲሱን የኢትዮጵያ የፍትህ፤ የነጻነትና የእኩልነት ታሪክ በደሙ ለመጻፍ የከተማ ኑሮ በቃኝ ብሎ የጫካና የበረሃ ኑሮዉን ተያይዞታል።
ዛሬ ይህንን እንዳባቶቹ ዱር ቤቴ ብሎና ጠመንጃቸዉን አንግቦ ከወያኔ ጋር ትንቅንቅ የጀመረዉን ህዝባዊ አርበኛ የብሄረሰብ ስብጥር የተመከለተ ማንም ሰዉ የአገራችን ኢትዮጵያ ዳግማይ ትንሳኤ ደጃፍ ላይ መሆኑን በሙሉ አፉ ደፍሮ መናገር ይችላል። ወያኔ በነጋ በጠባ ከሚያስረዉና የወደፊቱን ካጨለመበት ወጣት ጀምሮ ገዳማቸዉን ካፈረሰባቸዉ መነኮሳትና ቤ/ክርስቲያናቸዉን አስካረከሰባቸዉ ካህናት ድረስ የትግሉ ጎራ ሁሉንም አይነት ኢትዮጵያዉያን በብዛት አካትቶ ይዟል።
ወያኔ ስልጣን እንደያዘ በሚቆይባት በእያንዳንዷ ቀን ተጨማሪ ወጣቶች እንደሚታሰሩ፤ተጨማሪ ሰላማዊ ሰልፈኞች እንደሚገደሉ፤ተጨማሪ ጋዜጠኞች ሽብርተኞች ተብለዉ እንደሚታሰሩ፤ ተጨማሪ ምሁራን አገራቸዉን ለቅቀዉ እንደሚሰደዱና የአገራችን የኢትዮጵያም አንድነት የበለጠ እየላላ እንደሚሄድ ሁላችንም በሚገባ እናዉቃለን። በሌላ አነጋገር ወያኔ ስልጣን እንደያዘ የመቆየት አንድ ተጨማሪ ቀን በሰጠነዉ ቁጥር የኛም ሆነ የአገራችን ህልዉና በቀላሉ የማናበጀዉ እጥፍ ድርብ ችግር ዉስጥ ይወድቃል። ይህ እናት አገራችን ኢትዮጵያ ላይ የተደቀነዉ ችግርና መከራ ገና ከጧቱ የታያቸዉ ኢትዮጵያዉያን ባለፉት ሃያ አመታት የየራሳቸዉን እርምጃ ሲወስዱ ቆይተዋል። በዚህ ሂደት ዉስጥ አንዳንዶች ዉድ ህይወታቸዉን ገብረዋል፤ ሌሎች ደግሞ ታስረዋል፤ ተደብድበዋል፤ አገር ለቅዉ ተሰድደዋል። እዚህ ላይ አንድ ሁላችንም በትክክል ልንገነዘበዉ የሚገባን ሀቅ አለ፤ እሱም የኢትዮጵያ ችግር የአንድና የሁለት ሰዉ ችግር አይደለም፤ በአንድና በሁለት ሰዎች የሚፈታ ችግርም አይደለም። ኢትዮጵያ የሁላችንም አገር ናት፤ ችግሩም የሁላችንም ነዉ፤ ወያኔን በቆራጥነት ታግለን አገራችንን ከመበታተን ህዝባችንን ደግሞ ከዘረኝነትና ከድህነት ማላቀቅ ያለብንም እኛዉ ነን። ወያኔ ስለጠላነዉ፤ ስለሰደብነዉ ወይም ስለጮህንበት ብቻ በህዝብና በአገር ላይ በደል መፈጸሙን አያቆምም:፡ እነዚህ በደሎችና ችግሮች የሚቆሙትና የኢትዮጳያ ህዝብ የሰላም አየር መተንፈስ የሚችለዉ ወያኔ ከስልጣን ሲወገድና በምትኩ ኢትዮጵያዉያንን በእኩልነት የሚያስተናግድ መንግስት በኢትዮጵያዉያን ተመርጦ ስልጣን ሲይዝ ብቻ ነዉ።
የኢትዮጵያ ህዝብ ለሰብዓዊ መብቱ፤ ለነጻነቱና ለእናት አገሩ አንድነት መከበር ትናንት ካደረገዉ ትገል የዛሬዉ እጅጉን የሚያበረታታ ቢሆንም አሁንም ይህንን ህዝባዊ አደራ ከተሸከሙ ኃይሎች የሚጠበቅ ብዙ ስራ አለ። ከላይ ከፍ ሲል ደጋግመን እንደጠቀስነዉ ከወያኔ ጋር በሚደረገዉ የትግል ሂደት ዉስጥ የህዝብ ኃይሎች የሚመኩበት ትልቁ ኃይል ህብረታቸዉና ከጎናቸዉ የተሰለፈዉ የኢትዮጵያ ህዝብ ነዉ። የተቃዋሚ ኃይሎች አለመተባበርና አለመግባባት ከጎናቸዉ በተሰለፈዉ ህዝብ ዉስጥም አለመግባባትና አለመተባበር ይፈጥራል:፡ ዘረኛዉ የወያኔ አገዛዝ እየተቃወምነዉና እየታገልነዉ ዛሬ ድረስ የደረሰዉ እኛ ዉስጥ የነገሰዉ አለመተባበርና አለመግባባት እየረዳዉ ነዉ። ስለዚህ ዛሬ ወያኔን ለማስወገድ ብቻ ሳይሆን ወያኔ ከተወገደ በኋላም የሚገጥሙንን ዲሞክራሲያዊ ተቋማትን የመገንባትና ህዝባዊ ስርዐትን የመፍጠር አደራ ጭምር ለመወጣት በህብረትና በአንድነት መቆም አለብን። አንድነታችንና ህብረታችን አንድ ስራ ሰርቶ ወያም አንድ ነጣላ አላማ ከግብ አድርሶ የሚቆም ሳይሆን የእኛን ሀላፊነት ተወጥተን ለልጅ ልጆቻችን የምናስተላልፈዉ ብሄራዊ ቅርስ መሆን አለበት።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

lørdag 28. juni 2014

በአ.አ ዩኒቨርሲቲ 52 ተማሪዎች በ”ዲሲፕሊን” ሰበብ ፖለቲካዊ ክስ ተመሰረተባቸው (ዝርዝራቸውን ይዘናል)

(ዘ-ሐበሻ) በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመብት ጥያቄ አንስተው በሃገራዊ ጉዳይ ነቃ ያለ ተሳትፎ የሚያደርጉ 52 ተማሪዎች ላይ የዲሲፕሊን ክስ መመስረቱ ተሰማ። የዲሲፕሊን ክስ የተመሰረተባቸውን ተማሪዎች ስም ዝርዝር የያዘውን ወረቀት በማህበራዊ ድረገጾች ላይ የለቀቁት የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች ክሱ የተመሰረተባቸው ሰኔ 21 ቀን 2006 ዓ.ም ከጠዋቱ በ2 ሰዓት በተማሪዎች ጽ/ቤት እንዲገኙ ት ዕዛዝ ተሰጥቷል።
ምናልባትም እነዚህ በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ትኩረት አድርገው የሚንቀሳቀሱት ተማሪዎች ላይ በዲሲፕሊን ሰበብ ፖለቲካዊ እርምጃ ሊወሰድባቸው እንደሚችል የቅርብ ምንጮች ለዘ-ሐበሻ ያስታወቁ ሲሆን ዩኒቨርሲቲው ይህን እርምጃ ከወሰደ ሌላ የተማሪዎች አመጽ እንዲነሳ ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ታዛቢዎች ይናገራሉ።
በዲሲፕሊንክ ክስ ሰበብ የፖለቲካ እርምጃ ሊወሰድባቸው የተዘጋጁት ተማሪዎች ስምዝርዝር የሚከተለው ነው፦
students 1
students 2

fredag 27. juni 2014

ያገባኛል ባይነት እና ጋዜጠኝነት በአምባገነን ሥርዓት ውስጥ

ጋዜጠኛ ኤልያስ ገብሩ
1040ትናንት ሰኔ 14 ቀን 2006 ዓ.ም ሰማያዊ ፓርቲ ‹‹ያገባኛል ባይነት እና ጋዜጠኝነት በአምባገነን ሥርዓት ውስጥ›› በሚል ርዕስ እኔን ጋዜጠኛ አናንያ ሶሪ እና ዳዊት ሰለሞንን የውይይት መነሻ እንድናቀርብ በጋበዘን መሰረት በእኔ በኩል ለውይይት መነሻ ሀሰብ ይሆናሉ ብዬ ያቀረብኋቸውን ሶስት ነጥቦች እንዲህ አቅርቤያዋለሁ፡፡
በመጀመሪያ የሰማያዊ ፓርቲ ወጣቶች ጉዳይ ‹‹ያገባኛል ባይነት እና ጋዜጠኝነት በአምባገነን ሥርዓት ውስጥ›› በሚል ርዕሥ የውይይት መነሻ ሀሳብ ከሙያ አጋሮ ቼ ጋር እንዳቀርብ ስለጋበዘኝ በቅድሚያ ማመስገን እፈልጋለሁ፡፡

የሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ 29
ነሐሴ 15 ቀን 1987 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ-መንግሥት ሲጸድቅ የፈረሙበት የወቅቱ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ነበሩ፡፡ ይህ ሕገ-መንግሥት በአንቀጽ 29 (1) እና (2) ላይ ሃሳብን በነጻነት የመገለጽ መብትን በተመለከተ እንዲህ ይላል፡-

‹‹ማናኛውም ሰው ያለማንም ጣልቃ ገብነት የመሰለውን አመለካከት መያዝ ይችላል፡፡ ፣ማንኛውም ሰው ያለማንም ጣልቃ ገብነት ሐሳቡን የመግለጽ ነጻነት አለው፡፡ ይህ ነጻነት በአገር ውስጥም ሆነ ውጪ ወሰን ሳይደረግበት በቃልም ሆነ በጽሑፍ ወይም በሕትመት፣ በሥነ-ጥበብ ወይም በመረጠው በማንኛውም የማሰራጫ ዘዴ፣ በማንኛውም ዓይነት መረጃና ሐሳብ የመሰብሰብ፣ የመቀበልና የማሰራጨት ነጻነቶችን ያካትታል፡፡››

1012ባለፈው ዓመት መጨረሻ ላይ ከጓደኛዬ አቤል ዓለማየሁ ጋር
‹‹ኢትዮጵያን ማን ይታደጋት?›› በሚል ርዕስ ለንባብ ባበቃነው መጽሐፍ ውስጥ ይህን ሕገ-መንግሥት አስመልክቶ ዶ/ር ነጋሶን ቃለ መጠይቅ በማድረግ አነጋግረናቸው ነበር፡፡ ከላይ በመግቢያዬ የጠቀስኩት አንቀጽ 29 መከበር አለመከበሩ ከጥያቄዎቼ መካከል አንዱ ነበር፡፡ ዶ/ር ነጋሶም እሳቸው በምላሻቸው እንዲህ አሉ፡-
‹‹እንደ ጥሩ ምሳሌ የጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙን እና የእስክንድር ነጋን ጉዳይ መውሰድ እንችላለን፡፡ በዚህ አንቀጽ መሠረት፣ ርዕዮት እንደጋዜጠኛ የፈለገችውን ሐሳብ ጽፋ ለየትኛውም ሚዲያ የማቀበል መብት አላት፡፡ ይህ ተጥሶ ‹‹ከሽብርተኛ ድርጅት ጋር ግንኙነት አላት›› ተብሎ ተፈረደባት፡፡ እስክንድር ነጋ በአንድነት ፓርቲ ጽ/ቤታችን ድረስ በሕዝብ ግንኙነት ክፍል ተጋብዞ በመምጣት የቀረበውን ሐሳብ ከተሰብሳቢዎች ጋር ተቀምጬ አዳምጫለሁ፡፡ ሐሳቡን በመግለጹ ‹‹ሽብርተኛ ነው›› ተብሎ ተፈረደበት፡፡ እነ አቶ በቀለ ገርባ እና አቶ ኦልባና ሌሊሳ ‹‹ከአምነስቲ ኢንተርናሽናል ሰዎች ጋር ለምን ተነጋገራችሁ?›› ተብለው ነበር የታሰሩት፡፡ በተጨማሪም በአንድነት ፓርቲ ስር ትታተም የነበረችው የ‹‹ፍኖተ ነጻነት›› ጋዜጣ ያለመታተም ጉዳይ፣ የ‹‹ፍትሕ›› ጋዜጣ መታገድ፣ የ‹‹አዲስ ነገር›› እና የ‹‹አውራምባ ታይምስ›› ጋዜጦች የደረሰባቸውን ችግር እናውቃለን፡፡ አንቀጽ 29 እስከአሁን አልተከበረም፡፡››

1045እንግዲህ የተከበራችሁ የዚህ ውይይት ተሳታፊዎች፣ ሕገ-መንግሥቱ ላይ ፈርመው ያጸደቁት የቀድሞ ፕሬዚዳንት ሕገ-መንግሥቱ አለመከበሩን ጥቂት ምሳሌዎችን በማቅረብ ተናገርው ነበር፡፡ ይህ የሥርዓቱን ህገ ወጥነት እና አደገኝነት የሚያሳይ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ የጊዜው መንግሥታችን ‹‹ሀገርን የማስተዳድርበት ወርቃማ ሕግ አለ፡፡ ይህ ትልቅ ስኬታችን ነው›› በማለት ዘወትር ሲናገር እንዳደምጠዋለን፡፡ የኢህአዴግ መንግሥት የሕገ-መንግሥቱን አንቀጽ 29 በተለያዩ በርካታ ጊዜያትና በተለያዩ መንገዶች ሲንድ፣ ሲሸራርፍና ሲደፍር፤ ናድኩት፣ ሸራረፍኩና ደፈርኩት አይለንም፡፡ ይልቅ ጥቂት የማይባሉ ጋዜጠኞችን ‹‹ሕገ መንግሥቱን ለመናድ ሲንቀሳቀሱ … ከአሸባሪ ቡድኖች ጋር በመተባበር የሀገርን መሰረተ ልማቶች በሽብር ለማውደም ሲያሴሩ …ወዘተ በሚሉ ምክንያቶች ጠርጠሮ በመያዝ በፍርድ ሂደትም በተለያዩ ዓመታት የጽኑ እስራት ቅጣት በይኖባቸዋል፡፡ አሁንም በመሰል አካሄዶች ፖሊስ (በሽብርተኝነት ወንጀል) ሶስት ጋዜጠኞች እና ስድስት ጦማሪያን (ብሎገሮች)ን ‹‹ጠጥሬያቸዋለሁ›› በሚል በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ጣቢያ ከታሰሩ ከ56 ቀናት በላይ አልፏቸዋል፡፡ እነዚህ ጋዜጠኞች እና ጦማሪያን ሕገ-መንግሥቱን አክብረው የሚንቀሳቀሱ ነበሩ ብዬ በግሌ አምናለሁ፡፡ ዛሬም ሕገ-መንግሥቱን እና ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ሃሳቦችን አንስተን በጋራ ብንወያይ ወሳኝ ጉዳይ ይመስለኛል፡፡ መንግሥት ሕገ-መንግሥቱ በመናድ ብሎ ጋዜጠኞችን ፖለቲከኞችንና ዜጎችን በሕግ ተጠያቂ እንደሚያደርግ ሁሉ እሱም የሕገ-መንግሥቱን ድንጋጌዎች ሲንድ፣ ሲሸራርፍና ሲደፍር በሕግ እንዴት ተጠያቂ ማድረግ ይቻላል? በሚለው ላይ እንነጋገር እና የመፍትሔ ሀሳቦች ይንሸራሸሩ፡፡


ከሕገ-መንግሥቱ በፊት
10441001_ኢህአዴግ 1983 ዓ.ም ላይ የደርግ ሥርዓትን ከገረሰ በኋላ ነጻ ፕሬስ ማወጁ ብዙዎቻችንን የሚያስማማ እና ሊመሰገንበት የሚገባ ትልቅ እርምጃ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ነገር ግን፣ ሥርዓቱ ይህንን በማድረጉ ከሰማይ መና እንዳወረደ ተደርጎ መቆጠር አለበት አልልም፡፡ መንግሥት በተለያዩ ጊዜያት፣ በተለይ እራሱ ጠቅልሎ በያዛቸው እና እንደፈለገ በሚዘውራቸው ሚዲያዎች ነጻ ፕሬስ ማወጅ መቻሉን ከሚጠበቀው በላይ በማጋነን ለፕሮፖጋንዳ ፍጆታነት ሲጠቀምበት ተመልክተናል፡፡ ኢህአዴግ በትረ-ሥልጣን ባይይዝ ኖሮ ኢትዮጵያ ውስጥ ነጻ ፕሬስ ፈጽሞ አይታወጅም ብሎ መደምደምም ከባድ ነው፡፡ (እንዲህ ብለው የሚያስቡ ስላሉ ነው) በዚያን ጊዜ ከዓለም ነባራዊ ሁኔታ ጋር ለመሄድ ኢህአዴግ ነጻ ፕሬስን ማወጁ የውዴታ ግዴታውም ነበር – ከልቡ ቢያምንበትም ባያምንበትም፡፡
ከነጻ ፕሬሱ እወጃ በኋላ ባሉት ዓመታትም፣ እስከአሁን ድረስ የኢትዮጵያ ነጻ ፕሬስ በምን አይነት አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሲዳክር መጓዙን መናገር ለቀባሪ እንደማርዳት ስለሚሆን አልፈዋለሁ፡፡
አንድ ጉዳይ ግን በውስጤ ብዙ ጊዜ ይብሰለሰላል፡፡ እራሴንም ደጋግሜ ጠይቄ ለራሴ መልስ አግኝቼለታለሁ፡፡ የኢሕአዴግ መንግሥት የሕጎች ሁሉ የበላይ ሕገ መንግሥቱ ብቻ መሆኑን ደጋግሞ ነግሮናል፡፡ ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት ከሕገ-መንግሥቱ በፊት ቀዳሚ መሆኑ ይሰማኛል፡፡ ይህንን የምለው፣ ተፈጥሮ የሰውን ልጅ በነጻነት እንዲያስብ፣ ሐሳቡን ሐላፊነት በተሞላው መልኩ እንዲናገር፣ እንዲጽፍ፣ በተለያዩ ጥበባቶችና የመግባቢያ መንገዶች እንዲያስተላልፍ እና እንዲቀበል ቀድማ ለግሳዋለች፡፡ ይህንን የላቀ የተፈጥሮ ሕግ ከሕገ-መንግሥት ጋር ተሰናስሎ በሕግ ማዕቀፍ መደገፉ ጥቅሙ የላቀ መሆኑ አከራካሪ አይመስለኝም፡፡
በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ዓይነት አምባገነን ሥርዓቶችን ያየች ሀገር ቀላል የማይባሉ ዜጎች ተፈጥሯዊውንም ሆነ ሕገ-መንግሥታዊ የማሰብ፣ የመናገር፣ የመጻፍ …ወዘተ መብቶቻቸው ተሸብቦ በፍርሃት ቆፈን ውስጥ መውደቃቸውን አምናለሁ፡፡ ይህም ሥርዓታቱ (ደርግ የለየለት፣ ኢህአዴግ ደግሞ ዴሚክራሲያዊ ካባ የደረበ አንባገነን ነው) ለሥልጣናቸው ማቆያ እና ማራዘሚያ ሲሉ ከእነሱ ሃሳብ በተቃራኒው በሚያስቡ እና በድፍረት በሚናገሩ፣ በሚጽፉ …ዜጎቻቸው ላይ በሚወስዷቸው ኢ-ፍትሃዊ የግድያ፣ የድብደባ፣ የእስር፣ የእንግልት፣ የስደት …እርምጃዎች በዋነኝነት የሚመጣ ነው፡፡ አፋኝ የሆነው የጸረ-ሽብርተኝነት አዋጁም ኢትዮጵያኖችን ተፈጥሮ የለገሰቻቸውን የማሰብ፣ የመጻፍ፣ የመናገር …መብቶች በእጅጉ የሚጨቁን ነው ብዬ አምናለሁ፡፡
በመሆኑም ኃላፊነት በተሞላው መንገድ ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን በሕግ ማዕቀፍ ውስጥ አስገብቶ የማክበር እና የማስከበር ግዴታን እንዴት እንወጣው? በሚለው ላይ ብንወያይበት መልካም ነው ብዬ አስባለሁ፡፡


የእስረኞች አያያዝ እና ሰብዓዊ መብቶች
10483746_በሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ 18 (1) ላይ ‹‹ማንኛውም ሰው ጭካኔ ከተሞላበት፣ ኢ-ሰብዓዊ ከሆነ ወይም ክብሩን ከሚያዋርድ አያያዝ ወይም ቅጣት የመጠበቅ መብት አለው›› ይላል፡፡ ይህ ግን በተለያዩ ጊዜያት በማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ በግልጽ እየተጣሰ እንደሚገኝ እየደመጥን ያለነው፡፡ በዚያ ጭካኔ የተሞላበት ድርጊት ይፈጸማል፡፡ ‹‹እመኑ›› ወይም ‹‹በሌላ ሰው ላይ መስክሩ›› ተብሎ ቶርች ይደረጋል፡፡ ዜጎች ይደበደባሉ፣ ውስጥ እግራቸው ይገረፋል፣ ቀዝቃዛ ውሃ ይደፋባቸዋል፡፡ ‹‹ወፌ ላላ›› የተባለ አውጫጭኝ ግርፍ ሰዎች እንደሚገረፉ ይነገራል፡፡ ይሄንን ጋዜጠኛ አና ጦማሪ በፍቃዱ ሐይሉ፣ ጦማሪያኑ አቤል ዋበላ እና አጥናፍ ድብደባ እና ጥፊ የመብት ጥሰት እንደደረሰባቸው ለፍርድ ቤት ተናግረዋል፡፡ እኔም ለጥቂት ቀናት ማዕከላዊ ታሰሬ በነበረበት ጊዜ ከብዙ ታሳሪዎች ድርጊቱ እንደሚፈጸም አረጋግጫለሁ፡፡ እኔ ታስሬበት በነበረበት ‹‹8›› ቁጥር ውስጥ ከጎንደር የመጣ ብርሃኑ የተባለ ሰው በድብደባ ብዛት እያነከሰ ነበር የሚሄደው፡፡ ከደቡብ ሱዳን በሽብር ጉዳይ ተጠርጥረው ከተያዙት መካከል ከአንዱ የቀድሞ የጋምቤላ ክልል ፕሬዚዳንት (አቶ ኦኬሎ) በስተቀር መደብደባቸውን አረጋግጠውልኛል፡፡ የተደበበደቡትን የአካላቸውን ክፍል አሳይተውኛል፡፡ ለአራት ቀናት ያህል እንዲቆም የተቀጣ ወጣትም የደረሰበትን በመረረ መልኩ ነግሮኛል፡፡ በማንኛውም መንገድ ተጠርጥረው የተያዙ ዜጎች ሰብዓዊ መብቶቻቸው ሲጣስ ‹‹ያገባናል፣ ድርጊቱ ተገቢ አይደለም፡፡ ይህንን የሚፈጽሙ ግለሰቦች እና አካላት በሕግ መጠየቅ አለባቸው›› ብለን በድፍረት መናገር፣ የሚመለከተውን አካል መጠየቅና ድምጻችንን በተለያየ መንገድ ማሰማት ይገባናል፣ ለተግባራዊነቱም መንቀሳቀስ ይጠበቅብናል፡፡

በመጨረሻም በጣም በማከብራቸው ምሁር ፕሮፌሰር አለማየሁ ገብረማሪያም ሰኔ 13 ቀን 2006 ዓ.ም በነገረ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ላይ ‹‹ጋዜጠኞችንና ጦማሪያንን ማን ይፈራቸዋል?›› በሚል ርዕስ ለንባብ ካቀረቡት ጽሁፍ ውስጥ የማረከኝን ሀሳብ በመውሰድ የውይይት መነሻ ሃሳቤን እቋጫለሁ፡፡

‹‹ …ለእኔም ነጻ ጋዜጠኞች እና ጦማሪያን የሌሉበት ገዥ አካል ከሚኖር ወይም ደግሞ ገዥ አካል በሌለበት ነጻ ጋዜጠኞች እና ጦማሪያን ብቻ ከሚኖሩ የትኛው የተሻለ የሚል ምርጫ ቢቀርብልኝ የኋለኛውን ለመምረጥ ለሰከንድ እንኳ ጥርጣሬ አይኖረኝም፡፡ ከሁሉም በላይ ለዓላማ በጽናት የቆምኩ፣ ለምሰራው ትክክለኛ ሥራ ሁሉ ኩራት የሚሰማኝ፣ ላመንኩበት ዓላማ ከልብ እና በወኔ የቆምኩ፣ ዓላማዬን ለማስፈጸም በከባድ እርምጃ ወደፊት የምገሰግስ፣ ላልሰራሁት ወንጀል ይቅርታን የማልጠይቅ፣ በምሰራው ሥራ ሁሉ የማላፍር፣ ቆራጥ እና የማያወላውል ባህሪን የተላበስኩ የኢትዮጵያ ጦማሪ ነኝ፡፡››

ኃይል ለነጻ ጋዜጠኞችና የኢትዮጵያ ጦማሪያን!

ህወሓቶች የመቐለን ሰለማዊ ሰልፍ ለመከልከል ወስነዋል። (አብርሃ ደስታ)

mekeleትናንት ሐሙስ ማታ (ከምሽቱ 4:30) አንድ የህወሓት ባለስልጣን ደውሎ እንደነገረኝ ከሆነ ህወሓቶች የመቐለን ሰለማዊ ሰልፍ ለመከልከል ወስነዋል። ትናንት ማታ አስቸኳይ ስብሰባ የተጠራው “ሰልፉ በመቐለ እንዳይካሄድ፣ እንዳታዋርዱን፣ የህዝቡን ስሜት መረዳት እንዴት ያቅታችኋል? ነገሮች ሳይበላሹ ሰልፉ በሆነ ምክንያት እንዲቀር አድርጉ! ተብሎ ተደውሎልናል” ብሎ ነገረኝ። ማን ለማን ነው የሚደውልለት? አልነገረኝም። ግን ከአዲስ አበባዎቹ ይሆናል ብለን እንገምት።

ህወሓት ሰልፉን ለመከልከል ወስኖ ከሆነ በጣም የሚያሳፍር ተግባር ነው። ከመጠን በላይ ፈርቷል ማለት ነው። የመቐለ ህዝብ ሰልፍ የማድረግ መብቱ ተነፈገ ማለት ነው። ድሮምውም ኮ የህዝብ ስሜት የሚያጤኑ የደህንነት ሰዎች በዝተዋል። ህዝቡ እንደሚሰለፍ ስለተረዱ ይሆናል። መረጃው ትክክል ከሆነ በቃ የትግራይ ህዝብ ሰለማዊ ሰልፍ የማድረግ መብት የለውም ማለት ነው።
ግን ሰልፉን መከልከላቸው በደብዳቤ እስኪያሳውቁን ድረስ ሰልፉ እንደሚካሄድ ነው ታሳቢ የምናደርገው። ዉሳኔው ትክክል ስለመሆኑ የሚያረጋግጥ ደብዳቤ ያስፈልገናል። እውነት ግን ሰልፉ አይደረግም ብለው ደብዳቤ ሊሰጡን? አላምንም። ደብዳቤ ካልሰጡን ደግሞ ሰልፉ ይደረጋል። ስለዚህ እናያለን።
ደብዳቤው ከሰጡን ለሰልፉ መከለክል ምክንያቶች ለማወቅ ጓጉቻለሁ።

torsdag 26. juni 2014

ኦክስፎርድ፡ ኢትዮጵያ ከዓለም 2ኛዋ ድሃ አገር ናት

f78a1330f27fafbdf18deabc7e6add28_Mኢትዮጵያ ከ108 የዓለም ሃገራት በድህነት ከአፍሪካዊቷ ሃገር ኒጀር ቀጥላ ሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ  የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ጥናት ያመለከተ ሲሆን የኢኮኖሚ  ባለሙያዎች ሃገሪቷ ድሃ መሆኗ የሚስተባበል አይደለም ብለዋል፡፡ 

ሰሞኑን  ዩኒቨርሲቲው ይፋ ባደረገው የጥናት ውጤት፤ በኢትዮጵያ ከሚኖሩ ዜጎች 76 ሚሊዮን ያህሉ ድሆች ሲሆኑ በድሆች ብዛትም ከህንድ፣ ከቻይና፣ ከባንግላዴሽና ፓኪስታን ቀጥሎ ኢትዮጵያ  በ5ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች ብሏል፡፡ 

የድህነት መጠኑን በመቶኛ ስሌት ያስቀመጠው ጥናቱ፤ ኢትዮጵያ ከአጠቃላይ ህዝቧ 87.3 በመቶው ድሃ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 58.1 በመቶው ለኑሮው አስፈላጊ የሆኑ ነገሮች ያልተሟሉለት ምስኪን ተመፅዋች ዜጋ ነው ብሏል፡፡ ዩኒቨርሲቲው የአገራትን የድህነት ደረጃ የለካው የትምህርት፣ የጤናና የኑሮ ሁኔታዎችን መሰረት ያደረጉ አስር መስፈርቶችን  በመጠቀም ሲሆን፣ በአገሪቱ በገጠር ከሚኖረው ህዝብ 96.3 በመቶው፣ ከከተማ ነዋሪው ደግሞ 46.4 በመቶው  በድህነት አረንቋ ውስጥ እንደሚኖር በሪፖርቱ  ተመልክቷል፡፡ 

የድህነቱ መጠን በክልል ደረጃ ሲታይ፣ የሶማሌ ክልል 93 በመቶ ድሃ ህዝብ በመያዝ ቀዳሚ ሲሆን፤ ኦሮምያ በ91.2 በመቶ ሁለተኛ፣ አፋር በ90.9 በመቶ ሶስተኛ፣ አማራ በ90.1 በመቶ አራተኛ፣ ትግራይ በ85.4 በመቶ አምስተኛ ደረጃን ይዘው እንደሚገኙ ጥናቱ  ጠቁሟል፡፡ 20 በመቶ ድሃ ህዝብ ይኖርባታል ያላትን አዲስ አበባ ከአገሪቱ አነስተኛ ቁጥር ያለው ድሃ በመያዝ ቀዳሚ ያደረጋት ይሄው  ጥናት፣ ድሬደዋን በ54.9 በመቶ፣ ሐረርን በ57.9 በመቶ ሁለተኛና ሶስተኛ አድርጎ አስቀምጧቸዋል፡፡

 በሌላ በኩል የአፍሪካ ልማት ባንክ ከትናንት በስቲያ ባወጣው መረጃ፣ ኢትዮጵያ ባለፉት አስር  አመታት በአማካይ ከአስር በመቶ በላይ እድገት ማስመዝገቧን ሲመሰክር፣ የአውሮፓ ህብረት አምባሳደር ቻንታል ሄበርት በበኩላቸው፤ አገሪቱ የከፋ ድህነትን በመቀነስ ረገድ ስኬታማ መሆኗን ሰሞኑን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ መናገራቸው ተዘግቧል፡፡ 

የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲን የጥናት ሪፖርት በተመለከተ አስተያየታቸውን የጠየቅናቸው የቀድሞው የኢዴፓ ፕሬዚዳንትና የኢኮኖሚ ባለሙያው  አቶ ሙሼ ሰሙ በሰጡት ምላሽ፤“ረሃቡንና ጥማቱን እንዲሁም የኑሮ ውድነቱን በተጨባጭ እየኖርኩት ስለሆነ አውቀዋለሁ” በማለት የኢትዮጵያን  ድህነት  ለማመን የኦክስፎርድና የአይኤምኤፍ ሪፖርት አያስፈልገኝም ብለዋል፡፡ 
“የድህነት መለኪያው  መስፈርት ኢትዮጵያ ብቻ ሳትሆን ዓለም የተመዘነበት  ነው፤ በእርግጥም ውጤቱ  ኢትዮጵያን በትክክል ይገልፃታል” ያሉት አቶ ሙሼ ፤ዜጎች ራሳቸው ድህነቱን እየኖሩት ስለሆነ የማንንም ምስክርነትና ማስተባበያ አይፈልጉም ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ኢህአዴግ እንደተለመደው ሪፖርቱን ያወጡት የአገራችንን እድገትና ብልፅግና ማየት የማይፈልጉ ጠላቶቻችን ናቸው በማለት ራሱን ማታለል እንደሌለበት የገለፁት አቶ ሙሼ፤ መንግስት አገሪቱን ከድህነት ለማውጣት የተለየ መላ መዘየድ  እንዳለበት የኦክስፎርድ ጥናት  አመላካች ነው ብለዋል፡፡ 

ኢትዮጵያ ለውጥ ለማምጣት እያደረገች ያለውን እንቅስቃሴ ማንም አይክደውም ያሉት የኢኮኖሚ ባለሙያው፤“ሪፖርቱ የእኛን ፍላጎት ካላንፀባረቀ አንቀበልም የሚለው የተለመደ የኢህአዴግ ምላሽ   አያዋጣም፣ እንደውም ራሱን ለመፈተሽ የሪፖርቱን መውጣት እንደ መልካም አጋጣሚ ሊቆጥረው ይገባል” ሲሉ መክረዋል፡፡ 

በዜጐች መካከል ሰፊ የሃብት ልዩነት መኖሩን የጠቆሙት የኢኮኖሚ ባለሙያው ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ በበኩላቸው፤ “በኢትዮጵያ ድህነት አሁንም አለ” የሚባለው ትክክል ነው ብለዋል፡፡ “ትላልቆቹ የኢኮኖሚና የፋይናንስ ተቋማት- እነ ንግድ መርከብ፣ ቴሌኮም የመሳሰሉት በመንግስት ስር በመሆናቸው የሚያገኙት ገቢ መልሶ ለመሰረተ ልማት ነው የሚውለው፡፡ ለእያንዳንዱ ዜጋ የሚደርስበት መንገድ  የለም፡፡ የኢኮኖሚ እድገቱን በGDP (አጠቃላይ የምርት እድገት) ስንመለከተው፣ የድሃውን ህዝብ ትክክለኛ ህይወት እያሳየንም፡፡” በማለት ምሁሩ  አስረድተዋል፡፡
ፕሮፌሰር አማር ካስያን የሚባሉ ምሁር፣ የሰብአዊ  እድገት መለኪያ (human development indicators) ማውጣት አለብን በማለት ትምህርት፣ ጤናና  ረጅም እድሜ መኖር የሚሉ ሶስት መለኪያዎችን  እንደፈጠሩ የጠቆሙት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ ረጅም እድሜ የሚለው መለኪያ በምግብ ራስን መቻል ስለሚያካትት  እንደተባለውም ኢትዮጵያ ወደ ኋላ ቀርታለች ብለዋል፡፡ 
የሚሊኒየም የልማት ግቦች ተብለው የተነደፉትን በእርግጠኝነት እንደርስባቸዋለን፤ እንደውም እኔ ነበርኩ ስመራው የነበረው ያሉት ምሁሩ፤ “በእቅዱ እንደተቀመጠው ሁሉም ህፃናት ትምህርት ቤት የመግባት እድል አላቸው፣ ነገር ግን 1ኛ ደረጃን የመጨረስ እድላቸው የመነመነ ነው፡፡” በማለት በሚሊኒየም የልማት ግቡ የተቀመጠውን አሳክተናል ማለት የሰውን ልጅ ልማት አሳክተናል ማለት እንዳልሆነ ጠቁመዋል፡፡ 

በጤና ዘርፍም በርካታ የጤና ተቋማት  ተገንብተዋል፣ጥያቄው ግን በቂ ሃኪሞችና  የህክምና መሳሪያዎች ተሟልቶላቸዋል ወይ የሚለው ነው ያሉት ምሁሩ፤ እንዲያም ሆኖ በጤና መስክ መንግስት የሰራው ስራ የሚመሰገን ነው ሲሉ አድንቀዋል፡፡ 

በቅርቡ ወደ አድዋ ሄደው ያዩትና በሌሎች ክልሎች በስራ አጋጣሚ የተመለከቱት የድህነት ሁኔታ የሚዘገንን እንደሆነ ዶ/ሩ አልሸሸጉም፡፡ በመንግስት ሚዲያዎች “ህብረተሰቡን በጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ተጠቃሚ አድርገናል” የሚሉ ዘገባዎችን በተደጋጋሚ መስማታቸውን የጠቀሱት ምሁሩ፤ ጥያቄው እነዚህ ፕሮጀክቶች የምን ያህል ሰው ህይወት ቀይረዋል  የሚለው ነው ብለዋል፡፡ 
“ቻይና ባለፉት አምስት አመታት 5 ሚሊዮን ህዝብ ከድህነት  አውጥታለች፤ ሆኖም  ዛሬም ከአፍሪካ ህዝብ ብዛት የሚልቅ ድሆች አሏት፤ በነደፈቻቸው ስትራቴጂዎች ግን በፍጥነት ዜጐቿን ከድህነት እያወጣች ነው” ሲሉም ዋናው ጉዳይ ህዝቡን ከድህነት አረንቋ ማውጣት  እንደሆነ በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡ 

በእድገት ጉዳይ ላይ በአገር ደረጃ ግልጽ የሆነ ህዝባዊ ውይይት አለመኖሩን የተቹት ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ፤ መንግስት ኦክስፎርድ ዩኒቨርስቲ ያወጣው ሪፖርት ሃሰት ነው የሚል ከሆነ፣ ያንን  በተግባር ማረጋገጥ መቻል አለበት ብለዋል፡፡ 

የኦክስፎርድን ሪፖርት እኔም አንብቤዋለሁ፤ ነገር ግን ሪፖርቱን እንዴት እንደሰሩት አናውቅም ያሉት በገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሀጂ ኢብሳ፤ “እኛ እንደመንግስት ማንም እብድ ከመሬት ተነስቶ አጠናሁ ብሎ የሚያወጣውን አንቀበልም” ብለዋል፡፡ “የመረጃው አላማ ምንጩና መነሻው ምንድን ነው? የሚለውን አናውቅም፤ ከኛ ጋርም ግንኙነት የለውም”፡፡ በማለት መልሰዋል- ሃላፊው፡፡ “እኛ በሃገር ደረጃ ድህነት ምን ያህል ቀንሷል የሚለውን የምንለካው አለም በተቀበላቸውና በተስማማባቸው መለኪያዎች ተጠቅመን ነው” የሚሉት ኃላፊው፤ “ከድሮው በተለየ ከአለማቀፍ የገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ ጋር የኢትዮጵያ መንግስት ተቀራራቢ የሆነ የእድገት ሪፖርት እያወጣ መሆኑ የኦክስፎርድን ጥናት ተቀባይነት ያሳጣዋል” ብለዋል፡፡

ዩኒቨርሲቲው ከኒጀርና ከኢትዮጵያ በመቀጠል “የአለማችን ቀዳሚ ድሆች” ብሎ ያሰለፋቸው ስምንት አገራት አፍሪካ ውስጥ ሲሆኑ እነሱም  ማሊ፣ ቡርኪናፋሶ፣ ብሩንዲ፣ ሶማሊያ፣ መካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ላይቤሪያ፣ ጊኒና ሴራሊዮን ናቸው፡፡ 

ምንጭ- አዲስ ዜ

የወያኔን የጥፋት ድግስ እናምክን! June 26, 2014

ኢትዮጵያን የሚገዛው ጉጅሌ ሀገራችንን እየወሰደበት ያለው አደገኛ አቅጣጫ አሳሳቢ ከመሆን አልፎ የአደጋውን መራራ ፍሬ ማየት ከጀመርን ሰነበትን። የኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦች ወሳኝ ከሆነው የወደፊቱ የጋራ ጥቅማቸውና ህልውናቸው በበለጠ ልዩነታቸውና ያለፈ ታሪካቸው እንደዋናው ነገር እየተቆጠረ ለሚሰበከው ስብከት የኢትዮጵያ ህዝብ አስተዋይ ባይሆን ኖሮ እስካሁን ብዙ ጥፋት በደረሰ ነበር።
ህወሃት በህዝቡ ውስጥ የኖረውን ልዩነት የጠብ፣ የግጭትና የመፈራራት መሰረት በማድረግ በሥልጣን ላይ ለመቆየት ካለው ምኞት የተነሳ በመደዴ ካድሬዎቹ አማካኝነት ለዘመናት አብሮ የኖረውን ህዝብ በማቃቃር እኩይ ተግባር ላይ ተጠምዶ ይገኛል።
ህወሃት ይህን የማጋጨት ስራ በተለይ በስልጣን የመቆየት ፍርሃት ባባነነው ቁጥር የሚጠቀምበት መሳሪያ አድርጎታል። በባህርዳር ላይ የብሄረሰቦች ኳስ ጭዋታ ውድድር ምክንያት አድርጎ፣ መደዴ ካድሬዎቹን አሰማርቶ ስታዲዮም ውስጥ ኦሮሞዎች እንዲሰደቡ ካደረገ በኋላ ነገሩን ከማረጋጋት ይልቅ በኦሮሞኛ የቴሌቪዥንና ሬድዮ፣ ኦሮሞዎች በአማራዎች ተሰደቡ ብሎ ያስነገረው ለምንድን ነው? ከዚያ በኋላ በኦሮሚያ የተለያዩ አካባቢዎች ቁጣና ጠብ ለመቀስቀስ ብሎም በዚህ ጠብ ውስጥ ገላጋይ በመምሰል የአንዱ ብሄር ጠባቂ መስሎ ለመታየት ጉዳዩን ባልተረዱ የዋሆች ውስጥ ለመግባት ይፈልጋል። በአማራ ተወላጆች አካባቢ እኛ ከሌለን ኦሮሞ ይፈጇቹኋል፤ በኦሮምያም በሶማሊያም እንዲሁ በተዘጋ በር ውስጥ በተቃራኒው ዘረኝነትንና መከፋፈልን በመስበክ ንጹሃኑ ህዝብ ከፍርሃት ተነስቶ ተገዥ ደጋፊዎቹ እንዲሆኑ በማድረግ ላይ መሆኑንም ያልገባቸው የዋሆች ይኖራሉ። ህወሃትንና ባህርዩን በቅጡ ለምናውቀው ወገኖች ግን ይህ ተንኮሉ ትልቅ ሚስጥር አይደለም።
የጉጅሌው ቡድን የራሱን ስልጣንና የዝርፊያ ኢኮኖሚ ኮርቻ ለማደላደል እስከረዳው ወይም የሚረዳው መስሎ እስከታየው ድረስ ደሃ ገበሬዎችን ማፋጀትን፣ ህዝብን እርስበርስ ማናከስን፣ የቂም መርዝ መዝራትን የሚያየው እንደ ፖለቲካ ጥበብ ነው።
ጉጅሌው ብልጠት መስሎት የጎሰኝነትንና የማንነትን ደመነፍስ የሚነካ ፕሮፖጋንዳ በህዝቡ ውስጥ በመንዛት ሊያደርስ የፈለገው ጥፋት በአብዛኛው ህዝብ ዘንድ ስላልሰራለት የራሱን ሎሌዎችና ተካፋይ መደዴ ካድሬዎችን በማሰማራት የጭካኔ ስራዎችን በማካሄድ ላይ መሆኑን በብዙ መረጃዎች አረገጋግጠናል። በአሁኑ ወቅት በየቦታው የሚካሄደውን የህዝብ ማፈናቀልና ግጭት የሚመራው ራሱ ህወሃት ያሰማራቸው ካድሬዎች እንጂ በራሱ በህዝቡ ተነሳሽነት እንዳልሆነ ሁላችንም ልናውቅ ይገባል። በዚህ ሳይጣናዊ አካሄድ ለምትደርሰው ለያንዳንዷ ጉዳት ሀላፊነት የሚወስደውም ራሱ ህወሃት መሆኑን ግንቦት 7 አጥብቆ ያምናል።
ህወሃት መቃብር አፋፍ ላይ ሆኖ የሚደግስልንን የጥፋት ድግስ ለማምከን የየብሄረሰቡ ልሂቃን ሁሉ አንድ ላይ ሆነን ህዝባችንን እንድንታደግ ግንቦት 7 ለሁሉም የነጻነት ሃይሎች ጥሪውን ያቀርባል።
ግንቦት 7 በዚህ የህወሃት የጨለማ መንገድ ላይ የሚያበራውን የብርሃን ችቦ ይበልጥ በማብራት ላይ ይገኛል። ሁላችንም በምናገኘው የብርሃን ሃይል ጨለማው ላይ እያበራን ከማሳየት አልፈን ወደ መቃብሩ ልንገፋው ይገባል።
ግንቦት 7 በኢትዮጵያ የማንነትና የብሄር ብሄረሰብ ጉዳዮች በሰለጠነ መንገድ እና በመደማመጥ ሁሉንም ተጠቃሚ በሚያደረግ መንገድ መፍታት እንደሚቻል ያምናል። ይልቁንም የወደፊቱ የህዝባችንና የሀገራችን ጥቅም ይበልጥ የሚከበረው በስብጥርነታችን ላይ በምንገነባው አንድነት መሆኑን ያምናል።
የተከበራችሁ የአገራችን ዜጎች የነጻነታችን ጊዜ ቅርብ ነው። ህወሃት መቃብር አፋፍ ላይ ሆኖ ያዘጋጀልንን የጥፋት ድግስ፣ ሀገራችን የጋራ ጠላት በመጣባት ጊዜ ሁሉ እንደምታደርገው በአንድ ላይ ታግለን የጋራ ታሪክ እንሰራ ዘንድ የዘወትር ጥሪያችን እናቀርባለን።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!

የፊታችን ቅዳሜ በመቐለ የተቃውሞ ሰለማዊ ሰልፍ ይካሄዳል

አብርሃ ደስታ ከመቀሌ
ዓረና መድረክ ቅዳሜ ሰኔ 21, 2006 ዓም በመቐለ ከተማ የተቃውሞ ሰለማዊ ሰልፍ ያካሂዳል። ለሰልፉ የሚሆን ሙሉ ዝግጅት ተጠናቋል። የመቐለ ህዝብ በሰልፉ ለመሳተፍ ተዘጋጅቷል። ቅዳሜ ጥዋት ከአምስት ሺ በላይ ህዝብ ይሳተፋል ተብሎ ይጠበቃል ሰልፉ የጠራንበት ዋነኛ አጀንዳ መድረክ በአዲስ አበባና በክልሎች ዋና ከተሞች እያደረገው ካለው የተቃውሞ ሰለማዊ ሰልፍ አካል ሲሆን የሰልፉ ዋነኛ አጀንዳዎች ደግሞ የፍትህ እጦት፣ የነፃነት እጦት፣ የዉሃ ችግር፣ የሰብአዊ መብቶች ጥሰት፣ የመሬት ጉዳይ፣ የግብር ጉዳይ፣ የማዳበርያ ጉዳይ ወዘተ ናቸው።
ሰለማዊ ሰልፍ የማድረግ መብትም ሰለማዊ ሰልፍ በማድረግ ይረጋገጣል። የትግራይ ህዝብ እስካሁን ድረስ ሰለማዊ ሰልፍ የማድረግ መብቱ ተነፍጎ ይገኛል። በአላማጣ፣ ኲሓ፣ አይናለም፣ መቐለ (ገፊሕ ገረብ)፣ ሓውዜን፣ ዓዲግራት ወዘተ ዜጎች ሰለማዊ ሰልፍ ለማድረግ መክረው በፌደራል ፖሊስ ተደብድበዋል፣ ታስረዋል፣ ተገርፈዋል፣ ተገድለዋል። ስለዚህ ቅዳሜ ጥዋት ሰለማዊ ሰልፍ የሚጀመርበት ታሪካዊ ቀን ይሆናል። በመቐለ ታሪክ ለመጀመርያ ግዜ የተፈቀደ የተቃውሞ ሰለማዊ ሰልፍ ይደረጋል ማለት ነው።
ስለዚህ የመቐለው የተቃውሞ ሰለማዊ ሰልፍ ከዉሃ ጥያቄ የዘለለ ነው። የዉሃ ጥያቄ አንድ መሰረታዊ ጉዳይ ሁኖ ሌሎች አስቸኳይ መፍትሄ የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች አሉ። ሰዎች በመንግስት የፀጥታ ኃይሎች እየተገደሉ ነው። በሌሎች ክልሎችም እየተገደሉብን ነው። ንፁሃን ዜጎች ያለ ፍርድ እየታሰሩ፣ በድንጋይ እየተወገሩ፣ በፖሊስ እየተደበደቡ፣ በመርማሪዎች እየተገረፉ፣ ያለ ምንም ወንጀል በሽብር እየተከሰሱ ነው። ከዚህ በላይ የተቃውሞ ሰለማዊ ሰልፍ የሚጠይቅ ጉዳይ የለም።
ከሰብአዊ መብት ጥሰት፣ ከመገረፍ፣ ከመታሰር፣ ከመገደል በላይ ምን ሊያደርጉን ይችላሉ? በሌሎችስ ከዚህ በላይ ምን ተደረገ? ስለዚህ የተቃውሞ ሰለማዊ ሰልፍ ለማድረግ በቂ ምክንያት አለን። የመቐለ ህዝብ ሰለማዊ ሰልፍ የማድረግ መብቱ በሰለማዊ ሰልፍ ማክበር አለበት። የመቐለ ህዝብ እንደነ አዲስ አበባዎች፣ ባህርዳሮች፣ ደሴዎችና ሀዋሳዎች የተቃውሞ ሰልፍ የማድረግ መብቱ ሊከበርለት ይገባል።
የመቐለ ህዝብ ነፃነት ይፈልጋል። ስለዚህ ይሰለፋል። የቅዳሜ ሰልፍ በገዥው መደብ ካልተስተጓሆለ በቀር ኃይለኛ ሰልፍ ይደረጋል። በአደባባይ ስለሚደረግም ማንም ሰው አይቶ ይመሰክራል። የትግራይ ህዝብ የህወሓት ደጋፊ እንዳልሆነ ያስመሰክራል። ፎቶዎችና ቪድዮች እንቀርፃለን። ትመለከታላቹ።
ሰልፉ ቅዳሜ ጥዋት በ3:00 ሰዓት ከአደባባይ ዘስላሴ (ባዛር) ተነስቶ በሓውዜን አደባባይ አልፎ ሮማናት አደባባይ አቋርጦ አብርሃ ካስትል ሆቴል ከደረሰ በኋላ ወደ ናሽናል ሆቴል ታጥፎ በጤና ጣብያ በኩል ላዕለዋይ ፍርድቤት ደርሶ ሮማናት አደባባይ ላይ ይጨረሳል። የመድረክ መሪዎች ንግግር ያደርጋሉ። በ6:00 ሰዓት ይጠናቀቃል።
ህወሓት የሀዋሳውን፣ የባህርዳሩን፣ የአዲስ አበባውን ወይ የደሴውን ያህል ከፈቀደልን የቅዳሜ ሰልፍ በእርግጠኝነት የተዋጣለት ይሆናል። እስቲ ህወሓት ለትግራይ ህዝብ ሰልፍ ከፈቀደ እንይ። መቐለ ሰልፍ ልትጀምር ነው። ህዝብ ዓረና መድረክ ያለውን ድጋፍ ባደባባይ የሚገልፅበት ቀን: ቅዳሜ።
ህወሓት ሰልፉ እስኪጠናንቀቅ ድረስ ፀጥታ ካስከበረ ህወሓትን በፅሑፍ ነው የምናመሰግነው። ምክንያቱም የትግራይ ህዝብ እንደሌላው ህዝብ ሰለማዊ ሰልፍ የማድረግ መብቱ አስከብሮለታል ማለት ነውና። ሰለማዊ ሰልፍ መፍቀድ በራሱ ጥሩ ነገር ነው። ሰልፍ ለትግራይ ህዝብ ተአምር ነውና። ምክንያቱም ተፈቅዶልን አያውቅም።
እስቲ ህወሓት ትፈተን። እስቲ ህወሓት የህዝብ ድጋፍ አለኝ ብሎ የሚተማመን ከሆነ ሰልፉ እስኪጠናቀቅ ድረስ ሰልፉን ለማየት ዝግጁ ይሁን።mekele
ለማንኛውም ቅዳሜ እንገናኝ። የዉስጥ ለውስጥ ቅስቀሳው አልቋል። ነገ ዓርብ ፎርማል ቅስቀሳ ይደረጋል። በህዝብ ያለን ድጋፍ ለማወቅ ተከታተሉን።     

onsdag 25. juni 2014

በዓለም አቀፉ የሠላም ደረጃ ኢትዮጵያ ከ162 ሀገራት 139ኛ ደረጃን ያዘች

በየዓመቱ የየሀገራትን የሠላም ይዞታ በማጥናት ደረጃን የሚያወጣው ኢኒስቲትዩት ፎር ኢኮኖሚክስ ኤንድ ፒስ የተባለ ዓለም አቀፍ ተቋም የ2014 የዓለም ሀገራት የሰላም ደረጃ ከሰሞኑ የለቀቀ ሲሆን በዚህም ጥናቱ ከ162 ሀገራት ኢትዮጵያን በ139ኛ ደረጃ ላይ አስቀምጧል። ተቋሙ የአንድን ሀገር የሠላም ደረጃ ለማውጣት በርካታ የስኬት ማሳያዎች (Indicators) ግምት ውስጥ ያስገባል። ለዚሁ ልኬት ግብዓትነት ከሚውሉት መመዘኛዎች መካከል የውስጥና የውጭ ግጭቶች፣ አንድ ሀገር ከጎሬበቶቹ ጋር ያለው የግንኙነት ሁኔታ፣ የፖለቲካ አለመረጋጋት፣ የሽብር ተጋላጭነት፣ የወንጀል መስፋፋት እንዲሁም በእያንዳንድ አንድ መቶ ሺ ሰው በአንድ ሀገር ውስጥ ያለውን የእስረኛ ብዛትንም በመውሰድ ደረጃውን ለማውጣት በልኬትነት ይጠቀማል። ከዚህም በተጨማሪ ከአጠቃላይ ብሄራዊው ምርት አንፃር ለሚሊተሪው ዘርፍ የሚወጣውንም የገንዘብ መጠን ታሳቢ ያደርጋል። እነዚህንና ሌሎች ተጨማሪ ግብዓቶችን በማካተት ነው መረጃዎቹ ተተንትነው ደረጃ ወደ ማውጣቱ ስራ የሚካሄደው።
የየሀገራቱ ደረጃ ወጥቶ በድርጅቱ ድረገፅ እንዲሁም በዘ ኢኮኖሚስት መፅሄት ለህትመት የሚበቃ ሲሆን የዘንድሮውም ሪፖርት የ162 ሀገራትን መረጃ በመውሰድ ሰፊ ትንታኔ ከሰጠ በኋላ ኢትዮጵያ በ139ኛ ደረጃ አስቀምጧል። ተቋሙ በኤርትራና በኢትዮጵያ መካከል ሰላምም ሆነ ጦርነት የሌለበት ሁኔታ በመግለፅም በይደር የተቀመጠ ጉዳይ መሆኑንም አመልክቷል። ኢትዮጵያ ከፀጥታ ጋር በተያያዘም ከፍተኛ ገንዘብ የምታወጣ መሆኑን መረጃው ጨምሮ አመልክቷል። በዚህ የሀገራት የሰላም ደረጃ አይስላንድ የመጀመሪያውን ደረጃ በመያዝ በዓለም እጅግ ሰላም የሰፈነባት ሀገር ተብላለች። ዴንማርክ ሁለተኛ ስትሆን ኦስትሪያ የሶስተኝነትን ደረጃን ይዛለች።
ከ162ቱ ሀገራት 162ኛን ደረጃ በመያዝ በደረጃው ግርጌ ላይ የተቀመጠችው ሶርያ ናት። አፍጋስታን፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሱዳን፣ ኢራቅ፣ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎም በደረጃው የመጨረሻ ግርጌ ላይ የተቀመጡ ሀገራት ናቸው። ግብፅ 148ኛ ደረጃን ይዛለች።
ዓለም አቀፍ የሀገራት የሠላም ስኬት ደረጃ (Global peace Index) በኢንስቲትዩት ፎር ኢኮኖሚክስ ኤንድ ፒስ ተቋም በየዓመቱ ይፋ የሚሆን ሲሆን መረጃውን በማሰባሰቡ በኩል በርካታ ዓለም አቀፍ ተቋማት ሰፊ ትብብርና ተሳትፎን ያደርጋሉ። ከዓለም አቀፍ ተቋማቱ መካከል የተለያዩ የተባበሩት መንግስታት አካላትም ይገኙበታል። እንደ ኮፊ አናን እና ሊቀጳጳስ ዴዝሞንድ ቱቱን የመሳሰሉና በተለያዩ ጊዜያት ሀገራትን ከመሩ በኋላ የስልጣን ጊዜያቸውን ያጠናቀቁ መሪዎችም የሙያ አስተዋፅዖችን የሚያበረክቱበት ተቋም ነው። ተቋሙ የሀገራትን የሠላም ደረጃ የሚያወጣው 22 መስፈርቶችን አስቀምጦ በዚያ ልኬት መሰረት ነው።
ምንጭ – ሰንደቅ ጋዜጣ (በአዲስ አበባ የሚታተም)

የመጨረሻዉ መጀመሪያ

በቅርቡ በተከታታይ አገር ቤት ዉስጥ ቅርጽና ይዘት እየያዙ የምናያቸዉና ማንም አሌ የማይላቸዉ ግዙፍ እዉነታዎች ሁሉም በአንድነት የሚጠቁሙት አይቀሬዉ የወያኔ መጨረሻ መጀመሩን ነዉ። ከዚህ ቀደም በግልጽ እንዳየነዉ ወያኔ አንድ ቦታ ሲሸነፍ ሌላ ቦታ እያሸነፈ በጉልበትም በተንኮልም የፖለቲካ የበላይነቱን እንደያዘ ከሃያ ሁለት አመት በላይ ቆይቷል። ወያኔ ለአመታት ህዝብን ያታለለባቸዉ የዉሸት ክምሮችና ህዝባዊዉን ትግል ወደ ኋላ ለመጎተት የተጠቀመባቸዉ ስልቶች ዛሬ ሁሉም ሙጥጥ ብለዉ አልቀዉበት ዬኔ ነዉ ብሎ በሚመካበት ትግራይ ዉስጥ ጭምር መግቢያና መዉጪያዉ የጠፋዉ የተከበበ አዉሬ መስሏል። በያዝነዉ የ2006 ዓም ሁለተኛዉ አጋማሽ ወያኔ ጨካኙን የአግአዚ ኃይል እዚህም እዚያም አሰማርቶ ከሚቆጣጠራቸዉ ጥቂት አደባባዮች ዉጭ እንደቀድሞዉ በግልጽ ወጥቶ ወያኔን የሚያሞግስ ወይም የወያኔን የሌለ ገድል የሚናገር ሰዉ የለም። በሌላ በኩል ደግሞ በተለያዩ የትግል ስልቶች ወያኔን የሚታገሉ ኃይሎች አገር ዉስጥና ከአገር ዉጭ ኃይላቸዉና ቁርጠኝነታቸዉ እየጨመረ መጥቶ ወያኔ ያንን የተለመደ የቀቢፀ ተስፋ እርምጃዉን እዲወስድና የራሱን የመጨረሻ እሱ እራሱ ሳይወድ በግዱ እንዲያፋጥነዉ እያደረጉት ነዉ።
የአገራችንን አንድነት ሊያላሉና ኢትዮጵያ የሚለዉን ታሪካዊ ስም ከታሪክ ዉጭ ማድረግ ከሚችሉ አደገኛ የወያኔ ባህሪዮች ዉስጥ አንዱና ዋነኛዉ ዘረኝነቱና ለአገር አንድነትና ዳር ድንበር መከበር ያለዉ የግድየለሽነት ባህሪይ ነዉ። ዛሬ ወያኔ በአራቱም ማዕዘን በየቀኑ አየጨመረና እያየለ የሚሄደዉን የህዝብ ቁጣ ለማብረድና አፋፍ ላይ ለደረሰዉ ስርዐቱ ተጨማሪ ግዜ ለመግዛት የሚወስዳቸዉ እርምጃዎች ከዚሁ ከዘረኝነት ባህሪይዉ የሚመነጪ እርምጃዎች ናቸዉ። ወያኔ ዕድሜዉ ሊበረክት የሚችለዉ ለኢትዮጵያ ህዝብ መብትና ነጻነት የሚታገሉ ኃይሎች መግባባት ሲያቅታቸዉ መሆኑን ያዉቃል፤ ስለዚህም በተቻለዉ መጠን ኢትዮጵያዉያንን የሚለያዩና ግጭት ዉስጥ የሚከትቱ አጀንዳዎችን አየፈጠረ ይወረዉርልናል። ከእነዚህ አገር አጥፊ የወያኔ አጀንዳዎች ዉስጥ አንዱ ህዝብን በዘር ከፋፍሎ እርስ በርሱ እንዲጋጭ ማድረግ ነዉ። ለምሳሌ በቅርቡ ደቡብ ኢትዮጵያ ዲላ ከተማ ዉስጥ በንግዱ ህብረተሰብ ላይ የነጋዴዎችን አቅምና ትርፍ ያላገናዘበ ግብር በመጫን በአንድ በኩል ነጋዴዎቹ በዞኑ አስተዳዳሪዎች ላይ እንዲነሱ በማድረግ በሌላ በኩል ደግሞ የዞኑ አስተዳዳሪዎች ነጋዴዎቹን የምትሰሙን ከሆነ ስሙን አለዚያ ክልሉን ለቅቃችሁ ሂዱ የሚል አስነዋሪና የዜግነት መብትን የሚጋፋ መልስ እንዲሰጡ በመገፋፋት በጌዲኦ ብሄረሰብና በዲላና አካባቢዉ በብዛት በንግድ ስራ ላይ በተሰማራዉ የጉራጌ ማህበረሰብ መካከል ግጭት እንዲቀሰቀስ ለማድረግ ሞክሯል። ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ዉስጥም እንደዚሁ የጋምቤላ ህዝብ ከጋምቤላ ዉጭ ከሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎች የመጡትን ኢትዮጵያዉያን ክልሉ የእናንተ አይደለምና ለቅቃችሁ ዉጡ ብሎ እንዲያሰገድድ በመገፋፋት በኢትዮጵያዉያን መካከል ቂምና ጥላቻ እንዲፈጠር አድርጓል። ባለፉት አምስት አመታት ወያኔ ጋምቤላ ዉስጥ ገበሬዉን እያፈናቀለ መሬቱን ለዉጭና ለአገር ዉስጥ በተለይ ለትግራይ ባለኃብቶች በርካሽ ዋጋ ማስረከቡ የሚታወስ ነዉ። ይህ ባዕዳንን ጋምቤላ ላይ እያሰፈረ ኑና እረሱ እያለ የሚለምን ነዉረኛ አገዛዝ ነዉ ዛሬ ኢትዮጵያዉያንን ከጋምቤላ ዉጡ እያለ የሚያሰገድደዉ።
ዘረኛዉ የወያኔ አገዛዝ ደቡብ ኢትዮጵያ ዉስጥ ምን ያክል እንደተጠላ ለማወቅ ባለፈዉ ቅዳሜ መድረክ አዋሳ ዉስጥ የጠራዉን የተቃዉሞ ሰልፍ መመልከቱ ይበቃል። የአዋሳና የአካባቢዉ ህዝብ በዚህ መድረክ በጠራዉ የተቃዉሞ ሰልፍ ላይ የተገኘዉ ፌዴራል ፖሊስ፤ የክልሉ ፖሊስና የአገዛዙ ካድሬዎች በእያንዳንዱ ሰላማዊ ሰልፍኛ ላይ ያወርዱት የነበረዉን ዛቻ፤ ማስፌራሪያና ና የስድብ ናዳ ከምንም በለመቁጠር ነዉ። በዕለቱ የአካባቢዉን ሰላምና የሰልፈኛዉን ደህንነት አስጠብቃለሁ ብሎ በአዋሳ አደባባዮች ላይ የተሰማራዉ የወያኔ የፖሊስ ኃይል በህግ የተሰጠዉን ኃላፉነት ትቶ ፀረ ህዝብና ፀረ አገር እርምጃዎች ሲወስድ ታይቷል።
ወያኔ ብሶቱን አይቼ 17 ዐመት ታገልኩልት የሚለዉና ዛሬም እወክለዋለሁ ብሎ የሚነግረን ክልል ቢኖር የትግራይ ክልል ነዉ። ዛሬ ትግራይ ዉስጥም ወንድሞቻችንና እህቶቻችን የሞቱት ለዚህ አይደለም ብለዉ ብረት አንስተዉ ወያኔን አምርረዉ የሚታገሉ የትግራይ ወጣቶች ቁጥር ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ ነዉ። አስራ ሰባት አመት ሙሉ በወያኔ የማይጨበጥ ተስፋ ተታልሎ በከንቱ ህይወቱን የገበረዉ የትግራይ ወጣት ዛሬ እዉነቱ ገብቶት ወያኔን በትግራይ ህዝብ ስም መነገድህን አቁም እያለዉ ነዉ። በቅርቡ በመቀሌና በአካባቢዋ የታየዉ ከፍተኛ ፀረ ወያኔ እንቅስቃሴ የሚያሳየን ነገር ቢኖር ወያኔ ለዚህ የሸተተ ስርአቱ ዕድሜ ለመግዛት ቢፍጨረጨርም “ከወደቁ በኋላ መራገጥ ለመላላጥ” ካልሆነ በቀር ካሁን በኋላ ወያኔዎች በስልጣን ላይ መቆየት ቀርቶ የዘረፉትን ኃብት የሚያሸሹበት ግዜም ልንሰጣቸዉ አይገባም።
የወያኔ ጠመንጃና የሚቆጣጠራቸዉ የአፈና ተቋሞች አላናግር ወይም አላስተነፍስ እያሉት እንደ ማንኛዉም ኢትዮጵያዊ አንገቱን ደፍቶ እንዲኖር ስለተገደደ ነዉ እንጂ አመጸኞቹ የወያኔ መሪዎች ለተቀረዉ የኢትዮጵያ ህዝብም ሆነ ታገልንለት ብለዉ በስሙ ለሚነግዱት የትግራይ ህዝብ በፍጹም የማይበጁ ፀረ አገር ኃይሎች መሆናቸዉን የትግራይ ህዝብ ካወቀ ቆይቷል። ከቅርብ ግዜ ወዲህ ግን የትግራይ ህዝብም በቃ በስሜም አትነግዱ ወንድሞቼንና እህቶቼንም አትበድሉ ብሎ ደጋግሞ እየነገራቸዉ ነዉ። ዛሬ ብዙ የትግራይ ወጣቶች እዚያ የዛሬ ሰላሳና ሰላሳ አምስት አመት አባቶቻቸዉ የታገሉበት ጫካ ዉስጥ ገብተዉ እነሱም በተራቸዉ የዛሬዉን ዘረኛና አምባገነን አገዛዝ በጠመንጃ ጭምር በመፋለም ላይ ይገኛሉ። ወያኔ የመጨረሻ መደበቂያዬ ይሆነኛል ብሎ ይተማመንበት የነበረዉ የትግራይ ክልል ዛሬ ግልጽ በሆነ መልኩ የወያኔን መጨረሻ ለማየት የሚቸኩሉ ጀግኖች ክልል እየሆነ ነዉ።
የትግራይ ጫካዎችን ጨምሮ ሰሜን ኢትዮጵያ ዉስጥ ዘረኞቹ የወያኔ መሪዎች “ጨርቅ” ብለዉ ያንኳሰሱትን የኢትዮጵያ ባንዲራ በክብር አንግበዉ ከቋጥኝ ቋጥኝ የሚዘልሉት የትግራይ ህዝብ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ አርበኞች ወገንን የሚያኮሩ ዘረኞቹን የወያኔ መሪዎች ደግሞ ምነዉ ባልጀመርነዉ የሚያሰኙ የአገርና የወገን አለኝታ ሆነዋል። ዛሬ ወያኔ የትግራይን ምድር የእግር መረማመጃ እስኪጠፋ ድረስ በወታደርና በታንክ ያጠረዉ ይህንኑ በትግራይ ወጣቶች የተገነባ ህዝባዊ የነጻነት ኃይል ስለፈራ ነዉ። አምባገነኖቸ በደም የሚቀባበሉት የተፈጥሮ ባህሪያቸዉ ሆኖ ነዉ እንጂ የታንክና የወታደር ጋጋታ ህዝባዊ ኃይልን የሚያቆም ቢሆን ኖሮ እነሱ ዛሬ ሚኒልክ ቤ/መንግስት ዉስጥ ገብተዉ የኢትዮጵያን ህዝብ ሊረግጡ ቀርቶ ከተፈጠሩበት ደደቢት በረሃ ስንዝር ሳይራመዱ የእሳት እራት ሆነዉ ይቀሩ ነበር። ወያኔ ዛሬ በምድርና በአየር የታጠቀዉ መሰሪያና ሰራዊት ደርግ ከታጠቀዉ መሳሪያና ከነበረዉ ወታደራዊ ብቃት ጋር ሲወዳደር እዚህ ግባ የሚባል አልነበረም፤ ሆኖም ለነጻነቱ ቆርጦ የቆመን ህዝብ የሚገታ ምንም አይነት ምድራዊ ኃይል ሰለሌለ ወያኔ የኢትዮጵያን ህዝብ ድጋፍ አግኝቶ ደርግን መደምሰስ ችሏል። የዛሬዉ አምባገነን ወያኔም ዕድል ከደርግ የተለየ አይደለም። ወያኔ ያሰኘዉን ያክል ቢታጠቅ፤ ያሻዉን ያክል የድንበር አካባቢዎችን በታንክና በወታደር ብዛት ቢያጥር . . . . ደፋርና ጭስ መዉጪያ አያጣምና የወያኔ መሸነፍና መደምሰስ ጉዳይ ቀን እስኪያልፍ ያለፋል ካልሆነ በቀር ያለቀለት ጉዳይ ነዉ።
ደርግ ስልጣን በያዘባቸዉ የመጀመሪያዎቹ አምስት አመታት ዉስጥ ወታደራዊ አገዛዝ አንቀበልም ብለዉ ደርግን መግቢያና መዉጪያ ካሳጡት የህብረተሰብ ክፍሎች ዉስጥ ትልቁን ሚና የተጫዉተዉ ወጣቱ ትዉልድ ነበር። ይህ ወጣት ትዉልድ በኢትዮጵያ ህዝብ የዲሞክራሲ ትግል ዉስጥ ምን ግዜም ቢሆን ትዝታዉ የማይደበዝዝ አኩሪ የመስዋዕትነት ትግል ያካሄደና ያለምንም ፍርሃት ዉድ ህይወቱን ለኢትዮጵያ ህዝብ መብትና ነጻነት መከበር አሳልፎ የሰጠ ጀግና ትዉልድ ነዉ። ዛሬም አዲስ አበባ፤ አዋሳ፤ ባህርዳር፤ ጅማ፤ አምቦ ጊምቢና በተለያዩ የኢትዮጵያ ከተማዎች የሚኖረዉ ወጣት እኔም አገሬም አብረን ከምንጠፋ እኔ ሞቼ አገሬን አኖራለሁ በሚል ኢትዮጵያዊ እልህ ተነሳስቶ የወያኔን የመጨረሻ እያፋጠነ ነዉ። የወያኔን እገድልሃለሁና አጅ እቆርጣለሁ የሚል ዛቻ ከመጤፍ ሳይቆጥሩ በብዕራቸዉ ህዝብን እያስተማሩ ቃሊቲ ከገቡት ጀግኖች ጀምሮ ከተማ ዉስጥ ከወያኔ ጋር መኖር በቃኝ ብለዉ ጠመንጃቸዉን ተሸክመዉ ጫካ እስከገቡት ቆራጥ አርበኞች ድረስ ኢትዮጵያ ዳግም ትንሳኤዋን ለማብሰር የተዘጋጁ እልፍ አዕላፋት ጀግኖች አሏት።
በገጠሪቱ ኢትዮጵያም መሬቱን ተቀምቶ የተሰደደዉ ወጣት ልክ እንደ ከተማዉ ወጣት በወያኔ ላይ አምርሮ ዱር ቤቴ ብሎ ጫካ ከገባ ቆይቷል። አባቶቹና አያቶቹ ያቆዩለትን መሬት በወያኔ የተቀማዉ የጋምቤላ ገበሬ መሬቴን አለዚያም ህይወቴን ብሎ ወያኔን ማንቀጥቀጥ ከጀመረ አመታት ተቆጥረዋል። የሰሊጥ ማዕከል የሆነዉን ለምለም መሬቱን በወያኔ የተቀማዉና ዛሬም የአባቶቹን አጽም የተሸከመዉን መሬት ለባዕዳን ለመስጠት የሚዶለትበት የወልቃይት ጠገዴ ህዝብ በወያኔ ላይ ጥርስ ከመንከስ አልፎ ቃታ መሳብ ጀምሯል። እነዚህ ከትግራይ እስከ ጋምቤላ ከጋምቤላ እስከ ጎንደር በአራቱም ማዕዘናት የሚታዩ ህዝባዊ አመጾች የሚያሳዩን አንድ ትልቅ ነገር አለ፤እሱም ወያኔ በህዝብ የተጠላ ብቻ ሳይሆን ህዝብ አንቅሮ የተፋዉ ከቆሻሻም ቆሻሻ መሆኑን ነዉ።
ኢትዮጵያ ዉስጥ ዘረኝነት በጉልህ ከሚታይባቸዉና በዘረኝነት ፖሊሲ ላይ ተመስርተዉ ከተዋቀሩ አገራዊ ተቋሞች ዉስጥ አንዱና ዋነኛዉ የመከላከያ ተቋም ነዉ። የኢዮጵያ መከላከያ ተቋም በተለይ ዋናዉን የዉግያና አገርን የመከላከል ስራ የሚሰራዉ የሰራዊቱ ክፍል የተሰባሰበዉ ከመላዉ የአገሪቱ ክፍሎች ቢሆንም ይህ ተቋም ሁለት ፀረ ኢትዮጵያ የሆኑና ሆን ተብለዉ የጎደሉ ጉድለቶች አሉበት።አንደኛዉ ጉድለት ሠራዊቱን በተለያየ ደረጃ ከሚመሩና ከሚያዝዙ ወታደራዊ መኮንኖች ዉስጥ ከ95% በላይ የአንድ ዘር ተወላጆች መሆናቸዉ ሲሆን ሁለተኛዉ ትልቅ ጉድለት ደግሞ በኢትዮጵያ ሠራዊት ዉስጥ አግአዚ የሚባል የአዉሬዎች ክምችት የሚገኝበት አንድ ቋንቋ ብቻ የሚናገሩና ከአንድ ክልል የመጡ ተዋጊዎች ያሉበት ሠራዊት መኖሩ ነዉ። የአገሬን አንድነትና ዳር ድንበር አስከብራለሁ ብሎ ከተለያዩ አካባቢዎች የተሰባሰበዉ የኢትዮጵያ ሠራዊት በዘር ተከፋፍሎ የወያኔ መጠቀሚያ መሆን ሰልችቶታል።በተለይ ይህ ሰራዊት ብዛቱን በሚመጥን ቁጥር የመሪነትና የአዛዥነት ቦታ ስለማይሰጠዉ ሁል ግዜ በሚንቁትና በሚያንቋሽሹት የአንድ ቋንቋ ተናጋሪዎች መመራት አንገሽግሾታል። ዛሬ በየበረሃዉ ለሚገኙት የነጻነት አርበኞች እባካችሁ እንገናኝና አገራችንን አንድ ላይ ሆነን ነጻ እናዉጣ የሚል የትግል ጥሪ በተደጋጋሚ የሚመጣዉ ከዚሁ በዘረኝነት አለንጋ ከሚገረፈዉ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ነዉ። ከ1997ቱ ምርጫ በኋላ በተለይ ባለፉትሦስት አመታት በኢትዮጵያ ሠራዊት ዉስጥ ትልቁ የመወያያ አርዕስት አንዴት አድርገን የነጻነት እበኞችን እንቀላቀል የሚለዉ ጥያቄ ነዉ። በሠራዊቱ ዉስጥ ሆኖ በዚህ አርዕስት ላይ የማይወያይ የሰራዊቱ አባል ቢኖር እንደ ዘይትና ዉኃ ቅልቅል በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ዉስጥ ባዕድ አካል ሆኖ የሚታየዉ አዉሬዉ የአግአዚ ሠራዊት ብቻ ነዉ። አግአዚ ደግሞ የኢትዮጵያ ሰራዊት ሳይሆን በኢትዮጵያ ሰራዊት ዉስጥ እንደ እንክርዳድ የበቀለ ፍጹም ባዕድና ጨካኝ የሆነ የወያኔ መገልገያ ነዉ።
ከዚህ በላይ ለመጥቀስ እንደሞከርነዉ ወጣቱ፤ ገበሬዉ፤ ነጋዴዉ፤ ከተሜዉና ወታደሩ ሁሉም ወያኔን የሚቃወም ብቻ ሳይሆን ወያኔንና ዘረኛ ስርዐቱን ለመደምሰስ የተዘጋጁ `ኃይሎች ናቸዉ። ባለፈዉ ግንቦት ወር ወያኔ ዘረኝነትንና ሙሰኝነትን ኢትዮጵያ ዉስጥ የተከለበትን ሃያ ሦስተኛ አመት ሲያከብር የኢትዮጵያ ህዝብ የተዋርድንበትን ቀን አናከብርም ብሎ ወያኔ የራሱን በዐል ብቻዉን አክብሮ ዉሏል። ከዚህ በተጨማሪ እጅግ በጣም ብዙ ኢትዮጵያዉያን ይህንን የባርነት ቀን እንደገና ሲከበር ማየት አንደማይፈልጉ በይፋ ተናግረዋል። በእርግጥም ካሁን በኋላ ወያኔ ግንቦት ሃያን ብቻዉንም ቢሆን እንዲያከብር መፍቀድ የለብንም። ደግሞም ወደድንም ጠላን ወይም አወቅን አላወቅን ወያኔ ግንቦት ሃያን የሚያከብረዉ ብቻ ሳይሆን እንዳሰኘዉ ረግጦ የሚገዛን እኛ አሜን ብለን ስለፈቀድንለት ብቻ ነዉ። ህዝብ በአንድ ድምጽ አልገዛም ብሎ አለመገዛቱን የሚያሳይ እርምጃ መዉሰድ ቢጀምር አይደለም በዐል ማክበር ወያኔዎች ሰኞ ያደሩበት ሚኒልክ ቤ/መንግስት ዉስጥ ማክሰኞ ማምሸትም አይችሉም ነበር።
መሬት አልባዉ የኢትዮጵያ ገበሬ ወያኔ እስካለ ድረስ ልጆቼን ብሎ ስለወደፊቱ ማሰብ ቀርቶ የዕለት ጉርሱን የማግኘት ዋስትናም የለዉም። ነጋዴዉም እንደዚሁ ነዉ። ለወያኔ ሙሰኞች ካላጎበደደና ግማሽ ትርፉን ለእነሱ ካልገበረ ነግዶ መኖር ቀርቶ በልቶ ማደር የማይችልበት ግዜ እየመጣ ነዉ። ከተሜዉ ኢትዮጵያዊስ ቢሆን እስከመቼ ነዉ ሰላማዊ ልጆቹ ከጉያዉ እየተጎተቱ ሽብርተኞች ተብለዉ ዕድሜ ልክ ተፈርዶባቸዉ ቃሊቲ ሲገቡ የሚመለከተዉ? እስከመቼ ነዉ ዬት ገቡ ተብለዉ አድራሻቸዉ የጠፋ ልጆቹ መንገድና ህንጻ ሲሰራ የጅምላ መቃብራቸዉ በግሬደር እየተቆፈረ ሲወጣ የሚመለከተዉ? ከኢትዮጵያ ህዝብ አብራክ የወጡት የመከላከያና ፖሊስ ሠራዊት አባላት እስከመቼ ነዉ እነሱ እራሳቸዉ በወያኔ ዘረኝነት እየተለበለቡ ለወያኔ ዕድሜ መራዘም ሲሉ ወንድሞቻቸዉንናነ እህቶቻቸዉን የሚገርፉትና የሚያዋርዱት?
ወያኔ ኢትዮጵያ ዉስጥ ገዳማትን የእርሻ ቦታ አድርጓቸዋል፤ የእምነት ተቋሞችን የክፋቱ መሠረት አድርጓቸዋል፡ ምሁራንን ደግሞ አገራቸዉን ጥለዉ እንዲሰደዱ አድርጓል። ባጠቃላይ ወያኔ ያልበደለዉ፤ ያላሳቀቀዉ ወይም ተስፋዉን ያላጨለመበት የህብረተስብ ክፍል የለም። የገበሬዉ፤ የከተሜዉ፤ የነጋዴዉ፤ የወታደሩ ፤ የወጣቱና የምሁሩ ጠላት ወያኔ መሆኑን ካወቅን ዉለን አድረናል፤ ታዲያ ለምንድነዉ ይህንን የጋራ ጠላት በገራ የማናስወግደዉ? ከዛሬ በኋላ ወያኔ ስልጣን እንደያዘ በሚቆይባት በእያንዳንዷ ቀን የእኛ ስቃይና መከራ መብዛቱ ብቻ ሳይሆን ጥፋቱም የኛ መሆኑን አጥብቀን ልንረዳ ይገባል። ወያኔ እንደሆነ ቀንበር ለመሸከም የተመቻቸ ትከሻ ካገኘ ምን ግዜም ቢሆን ከመግዛት፤ ከማሰርና ከመግደል ወደ ኋላ አይልም። አልገዛም፤ አልታሰርም ወይም አትገድሉኝም ብሎ በወያኔ ላይ መነሳት የዚህ ትዉልድ ኢትዮጵያዉያን ሀላፊነት ነዉ፤ ይህ ሀላፊነት ደግም በህብረት ቆመን ለአንድ አላማ በአንድነት ከታገልን በቀላሉ ልንወጣዉ የምንችለዉ ሀላፊነት ነዉ። ሰለዚህ የዛሬም ጥሪ እንደትናንቱ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ወያኔን ለማስወገድ ሀላፊነቱን ይወጣ የሚል ነዉ።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!

tirsdag 24. juni 2014

ሰበር ዜና ጅዳ ሳውዲ አረቢያ አንዲት ኢትየጵያዊት በጁዳ ቆንስል ግቢ ታንቃ ተገኘች

unnamed (1)በሳውዲ አረቢያ ጅዳ ቆንስላ ጽ/ቤት ግዜያዊ የስደተኞች መጠለያ ውስጥ እንዲት ኢትዮጵያዊት ታንቃ መገኘቷ የአካቢውን ማህበረሰብ ደረት ሲያስደቃ መዋሉን ቦታው ላይ የነበሩ የአይን እማኞች አረጋግጠዋል። ዛሬ በኢትዮጵያ ሰአት አቋ ጣጠር ከቀኑ 10 ሰአት ቆንስላው ጽ/ቤት ግቢ ውስጥ ታንቃ የተገኘቸው ወጣት በ 20 አመት የእድሜ ክልል ውስጥ የምትገኝ መሆኗን የሚናገሩ እማኞች በኮንተራት ለስራ መጥታ ከአሰሪዎቾ ባለመስማቷ በጅዳ የኢትዮጵያ ቆንስላ ግዜያዊ መጠለያ ኮንቴነር ውስጥ ለረዥም ወራት ስትሰቃይ የኖረች ሳትሆን እንደማትቀር ይናገራሉ ; ፡ በኢትዮጵያ ሰዓት አቋጣጠር ዛሬ ከቀኑ 10 አካባቢ እዚህ ቆንስላ ግቢ ውስጥ የታነቀቸውን ወጣት በአይናቸው ለማየት እድል ያገኙ እማኞች ወጣቷ እራሷን አንቃ ለመግደል ስትወራጭ አንገቷ ውስጥ የገባው ገመድ መስል ነገር ጉሮሮዋን ቆርጧ ወዲያው ሳይገድላት እንዳልቀረ ይገልጻሉ።

ይህ ዜና እስከ ተጠናከረበት ግዜ ድረስ የወጣቷ ሬሳ አለመንሳቱን የሚናገሩ ምንጮች በአካባቢው የፓስፖርተ እድሳት እና መስል ተዘማጅ ጉዳዩቹን ለማስፈጸም የቆንስላ ግቢውን አጨናነቀው እምባ ሲራጭ የነበሩ ኢትዮጵያውያን ከቆንስላው ጽ/ቤት እንዲወጡ መደረጋቸውን የአይን እማኞቹ አክለው ገልጸዋል ። ይህ በዚህ እንዳለ የሬሳ ጉዳይ የሚከታተለው እና የቀድሞ የኮሚኒቲ አመራር አቶ መሃመድ ሸህ ተፈቅዶለት ወደ ግቢው ሲገባ ያዩ ምንጮች ቦታው ላይ የሳውዲ ፖሊሶች እና ዲፕሎማቶች መገኘታቸውን አረጋግጠዋል ። የጅዳ ቆንስ ጽ/ቤት የእህቶቻችንን አስከሬን ሲያስተናገድ የመጀመሪያ ግዜው እንዳለሆነ የሚናገሩ ወገኖች በዲፕሎማቱ የአሰራር ድክመት በአንድ ወር ውስጥ ብቻ ለሁለተኛ ግዜ ታንቃ ህይወቷ ባለፈው ወጣት ተደናግጠው ሲጮጮሁ በነበሩ ኢትዮጵያውያን የቆንስላው ጽ/ቤት ድባብ ወደ መቃብር ስፍራ ነት ተለውጦ ማምሸቱን ይናገራሉ ።

በአሁኑ ግዜ በዚህ የቆንስላ ቅጥር ግቢውስጥ ከ 40 የሚበልጡ ተፈናቃይ የኮንተራት ሰራተኞች ከሰው እይታ ተገለው ይሚገኙ ሲሆን ባዶ ክፍሉ ውስጥ ያለምንም እርዳታ ሃገር ትገባላቹ በሚል ተስፋ መጋዘን ተቆልፎባቸው ለበለጠ ስቃይ እና መከራ እይተዳረጉ ከሚገኙ እህቶቻን መሃከል አብዛኛዎቹ የፈላ ውሃ በአሰሪዎቻቸው የተደፋባቸው የተድፈሩ እና ደሞዛቸው የተነጠቀ መሆኑ ይነገራል።፡፤ የወገኖቻችን ሞት ከሚፈበረከበት ሁለተኛው ማዕከል ጅዳ ከሆነው የ ቆንስላ ጽ/ቤት ግቢ ውስጥ በአንድ ወቅት አንድ የውሃ ጉድ ጓድ ውስጥ ሬሳዎ በተገኘ ኢትዮጵያዊት ጉዳይ የህ.ወ.ህ.ቱ አባል አቶ ገሬ ለወራት ወህኒ ቢወርዱም የሞቾ ምስኪን ጉዳይ ተድበስብሷ ሲቀር አቶ ገሬ ከወራት እስራት በኋላ በወጭ ጉዳይ ግፊት መፈታታቸው በህዝብ ዘንድ ተቃውሞ ማስነሳቱ አይዘነጋም።
Ethiopian Hagere ጅዳ በዋዲ

በሀዋሳ በእስር ላይ የሚገኙት የአንድነት ፓርቲ አባላት ዛሬም የረሀብ አድማ ላይ ናቸው!! በሀዋሳ ሰ.መ.ጉ እስረኞችን እንዳይጎበኝ ተከለከለ – የሚሊዮኖች ድምጽ ለነጻነት

አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ(አንድነት)ባሳለፍነው ሳምንት ሰኔ 15 ቀን 2006ዓ.ም በሃዋሳ ከተማ ሊያካሂድ የነበረውን ሰላማዊ ሰልፍ ተከትሎ በእስር ላይ የሚገኙት የአንድነት ፓርቲ አባላት ‹‹ፍትህን ተነፍገን ትግላችን አይቆምም ››በማለት ዛሬም ለ4ኛ ቀን በርሀብ አድማ ላይ ናቸው፡፡አባላቱ በቁጥጥር ስር ከዋሉበት ቅዳሜ እለት ጀምሮ በረሀብ አድማ ላይ ሲሆኑ በትላንትናው እለት ሰኞ ሰኔ 16 ቀን 2006 ዓ.ም በሀዋሳ ከተማ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቀርበው በኢ/ፌ/ዲ/ሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 27(1-ሀ)32/1-ሀ/እና 257 ላይ የተመለከተውን በመተላለፍ በሚል የአዋሳ ከተማ ከፍተኛ ዐ/ሕግ ክስ ተመስርቶባቸው የዋስትና መብታቸው ተነፍጎ በእስር እንዲቆዩና ዓቃቤ ህግ ምስክሮቹን ለሰኔ 20 ቀን 2006 እንዲያሰማ ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ በማስተላለፉ ወደ እስር ቤት እንዲመለሱ ተደርጓል፡፡
በተያያዘም ዜና ሰ.መ.ጉ በሃዋሳ ከተማ በእስር ላይ የሚገኙትን የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ አባላትን ሁኔታ ለመመልከት ወደ ወደ ሃዋሳ እስር ቤቶች ያመሩት የሰብዓዊ መብት ጉባዔ ሀላፊዎች እስረኞቹን ለማግኘት እንደማይችሉና ከማንም ጋር እንዳይገናኙ ትዕዛዝ በመተላለፉ ምክንያት ታሳሪዎቹን ማግኘት እንዳልተቻለና የጣቢያ ሀላፊዎቹን ለማናገር የተደረገውም ጥረት እንዳልተሳካ አስረድተዋል፡፡10448208_657204214364516_9050720156707149922_n
10450753_657204294364508_6267425299544943631_n

søndag 22. juni 2014

የ2007 የመንግሰት በጀት ሚስጥር

ግርማ ሰይፉ ማርይ
(የኢትዮጵያ ፓርላማ አባል)

የኢትዮጵያ በጀት በደንብ አድርጎ ለመረመረው ሀገሪቱ ያለችበትን ፖለቲካ ሁኔታ የሚያሳይ ነው፡፡ ይህም ማለት በበጀቱ ውስጥ የቻይና፣ ምዕራባዊያን ሀገሮች እንዲሁም የምዕራብ ሀገሮች ይዞታ የሚባሉት አለም አቀፍ ባንኮች እጅ በግልፅ የሚታይ ነው፡፡ እንደምታውቁት መንግሰት ለ2007 ዓመተ ምህረት ያቀረበው በጀት ብር 178.6 ቢሊዮን ነው፡፡ ዘጠኝ ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር አካባቢ ማለት ነው፡፡ መደበኛው ወጪ እና የክልሎች ድጋፍ ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ የሚሸፈን ሲሆን ዋና ዋና የካፒታል በጀት ደግሞ ከመደበኛ ወጪ እና ክልሎች ድጋፍ ከሚተርፈው አነሰተኛ የሀገር ውስጥ ገቢ እና ለበጀት ጉድለት ለመሸፈን ከታሰበው ከሀገር ውስጥ ባንኮች ብድር ይሸፈናል ተብሎ የሚጠበቅ ነው፡፡ ከአጠቃላይ በጀቱ 19.2 በመቶ ከእርዳታና ብድር ይሸፈናል በዝርዝር ሲታይ ግን የመደበኛ በጀቱ 21.8 ከመቶ፣ የካፒታል በጀቱ ደግሞ 36.5 ከመቶ የሚሸፈነው ከብድርና እርዳታ ነው፡፡
ስንት ሰው እንደሚያስታውስ ባላውቅም የቀድሞ አዲስ ጉዳይ ጋዜጣ (ሁሌም ጋዜጣ ሳስብ የሚናፍቀኝ) በአንድ ወቅት የቀረበን በጀት ይህ በጀት ኢትዮጵያዊ በጀት ነው ወይ? የሚል ጥያቄ አንሰቶ ነበር፡፡ የበጀትን ዜግነት የጠየቀበት ገፊ ምክንያት በዚያን ሰሞን መወያያ፤ በአሁኑ ጊዜ ጠርናፊ ህግ የሆነውን የሲቪል ማህበራት ህግ ነበር፡፡ ይህ አፋኝ ህግ ማነኛውም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀስ ሰቪል ማህበር በጀቱ ከአስር በመቶ በላይ ከውጭ ከሆነ ኢትዮጵያዊ አይደለም ነው የሚለው፡፡ አሁን በሀገራችን የሚንቀሳቀሱት ብዙዎች መንግሰታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የተመዘገቡት በኢትዮጵያዊነት ሳይሆን “ረዚደንት” በሚል ቅፅል ነው፡፡ አዲስ ጉዳይ ጋዜጣ ይህን በጠየቀበት ወቅት የሀገሪቱ በጀት ከ40 በመቶ በላይ ከውጭ እርዳታ ሰለነበር ይህ መንግሰት ይህን ያህል ከውጭ የሚያገኝ ከሆነ ኢትዮጵያዊ አይደለም የሚል መከራከሪያ ይዞ ወጥቶ ነበር፡፡ ይህን ሰፋ አድርገው በመተርጎም አንድ አንድ ሰዎች የገቢ ምንጭ ዜግነት የሚወስን ከሆነ ብዙ ኢትዮጵያዊያን ከውጭ ከሚኖሩ ዘመዶቻቸው በሚላክላቸው ገንዘብ የሚተዳደሩ ስለሆነ ዜግነታቸው ኢትዮጵያዊ መሆን የለበትም ብለው ነበር፡፡ ስላቅ መሆኑ ነው፡፡ ያለበለዚያ ደግሞ የሚልኩላቸው ዘመዶቻቸው ዜግነት ያልቀየሩ በመኖሪያ ፍቃድ (ረዚደንት) የሚኖሩ መሆናቸውን ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል፡፡
ethiopia-parliament
የሰዎችን ወይም የድርጅቶችን ዜግነት ኢትዮጵያዊ ወይም የውጭ ለማድረግ የገቢ ምንጭ መስፈርት መሆን የለበትም የሚለውን መከራከሪያ መንግሰት በዋዛ ያለፈው እንዳይመስላችሁ፡፡ መፍትሔ ብሎ የያዘው በተቻለ መጠን መንግሰት በጀቱን በመከፋፈል እና የተወሰኑት ወደ ጎን በማድረግ የብድርና የእርዳታ ገንዘቡ እንዳይታይ ማድረግ ነው፡፡ ለዚህም ነው መንግሰት ከፍተኛ መዋለ ንዋይ ከሚፈስባቸው የመሰረተ ልማቶች ውስጥ ዋና ዋና የሆኑትን ለምሳሌ እነ ቴሌ፣ መብራት ሀይል፣ ባቡር፣ የመሳሰሉት በሪፖርት ውሰጥ በስፋት እንደሰኬት ተካተው በበጀት ውስጥ ግን አይታዩም፡፡ ሉሎች ፋብሪካዎች ለምሳሌ ስኳር ፋብሪካ፣ ማዳበሪያ ፋብሪካ የመሳሰሉት ትልልቅ የመንግሰት ፕሮጀክቶቸ በበጀት ውስጥ የሉም፡፡ እነዚህ ከፍተኛ መዋለ ንዋይ የፈሰሰላቸው የመንግሰት ኢንቨስትመንቶች ከበጀት ውሰጥ እንዲወጡ የተደረጉት ደግሞ ብዙዎች በብድር የሚሰሩ ናቸው፡፡ የእነዚህ ፕሮጀክቶች የብድር ሂሣብ በበጀት ውስጥ ቢደመር የመንግሰትን በጀት ዜግነቱ ኢትዮጵያዊ ላይሆን ነው ማለት ነው፡፡ ለነገሩ በሲቪል ማህበራት ትርጉም እነዚህ ሁሉ ተቀንሰው አሁን የቀረበው የመነግሰት በጀት ኢትዮጵያዊ በሚያደርገው ደረጃ ላይ አይለም፡፡ ምክንያቱም ከአጠቃላይ በጀቱ 19.2 በመቶ ከውጭ ብድርና እርዳታ የሚገኝ ስለሆነ ማለት ነው፡፡
መንግስት በበጀት ውስጥ ያካተታቸው በእርዳታና ብድር የተገኙ አብዘኞቹ የካፒታል ወጪዎች ለኤኮኖሚ ሴክተር መንገድ፣ ግብርና እና ውሃ ሲሆን፤ እርዳታው ደግሞ ለጤናው ሴክተር የተመደበ ነው፡፡ የእነዚህ ገንዘቦች ዋናኛ ምንጮች ደግሞ የኒዎ ሊብራል አራማጆች የሚባሉት መንግሰታት እና የእነዚሁ መንግሰታት ይዞታ ናቸው የሚባሉት ባንኮች የሰጧቸው ብድሮች ናቸው፡፡ እነዚህ መንግሰታት እና በቁጥጥራቸው ስር ያሉት የፋይናንስ ተቋማት ኢትዮጵያዊያን ጤናቸው እንዲጠበቅ የተሻለ መንገድ እንዲኖረን፣ ምርታማ ግብርና እንዲሁም ንፁህ ውሃ እንዲኖረን ዕርዳታና ብድር እየሰጡን፤ በሌላ በኩል ደግሞ ብጥብጥ እንዲነሳ የቀለም አብዮት ይደግፋሉ ብሎ ስጋት ውስጥ መውደቅ አይቃረንም ወይ? ይህ በእውነት የአብዮታዊ ዲሚክራሲ ወይም የልማታዊ መንግሰት ቅዠት ይመስለኛል፡፡
በጣም የሚያስገርመው ደግሞ በዋነኝነት ከፍተኛ እርዳታ የሚሰጡን መንግሰታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች በኩል አድርገው በቀለም አብዮት ሊያጠፉን ነው የሚባሉት የኒዎ ሊብራል አራማጅ ተብለው የተፈረጁት ሀገሮች መንግሰታት ናቸው፡፡ ከነዚህ ውሰጥ ቻይና እንደ መንግስት የምትሰጠን እርዳታ በሀገር ውስጥ ከውጭ ሀገር ዜጎች ምዝገባና የስራ ፈቃደ ከምናገኛው ያንሳል፡፡ ከሌሎቹ ሀገራት ጋር ሲነፃፀር ደግሞ ከአንድ መቶኛ ያነሰ ነው፡፡ ቻይና ሀገራችን በበጀት ውስጥ ከተካተተው ብድር ከ59 በመቶ በላይ ሰጥታናለች፡፡ ይህ ቻይና የሰጠችን ብድር ብዙ ስለሆነ ሳይሆን መንግሰታት ለኢትዮጵያ የሰጡት ብድር እጅግ ዝቅተኛ ከመሆኑ የመጣ ከፍተኛ የመቶኛ ድርሻ ነው፡፡ ቻይና በጀት ውስጥ ባልገባው ብድር ከፍተኛ አበዳሪያችን ነች፡፡ የቻይና ብድር በዋነኝነት በበጀት ውስጥ ባለተካተቱት ከፍተኛ የመንግሰት የመሰረተ ልማቶች እና የኤኮኖሚ ሴክተሮች ላይ ነው፡፡ ለምሳሌ ከበጀት እንዲወጣ የተደረገውን የቴሌን ማስፋፊያ ብቻ ብንወሰድ ወደ 32 ቢሊዮን ብር ወይም 1.6 ቢሊዮን በላይ የአሜሪካን ዶላር በ2007 በጀት ተብሎ የተያዘውን 18 ከመቶ ይሆናል፡፡ ይህ ገንዘብ በጀት ውስጥ ቢታይ እና የመንግሰትን የዜግነት መስፈርት ብንጠቀም መንግሰት ኢትዮጵያዊ ነው ለማለት ይቻላል ወይ? በጀት የመንግሰትን አቅም የሚያሳይ መለኪያ ነው በሚለው ልማዳዊ መለኪያ ለመጠቀም ለሚፈልግ ለቀጣይ ዓመት የቀረበው በጀት ትክክለኛውን የመንግስት ጡንቻ የሚያሳይ ነው ብለን ለመውሰድ እንቸገራለን፡፡
የኢኮኖሚና ፋይናንስ ሚኒሰትሩ አቶ ሶፊያ አህመድ በዚህ ጉዳይ በተደጋጋሚ በግንባር ቀደምነት የሚያነሱት የኢትዮጵያ አየር መንገድን ነው፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዕዝ ኢኮኖሚ በሚባለው በደርግም ጊዜ ቢሆን ሪፖርቱን በይፋ ያቀርባል አቶ ሶፊያ ግን ይህን እንዲያደርግ ያለበትን ዓለማ አቀፋዊ ጫና የምንረዳ አይመስላቸውም፡፡ ያለበለዚያ ቦይንግ መግዣ ገንዘብ ሊገኝ እንደማይችል ግልፅ ነው፡፡ አሁን እኛ የግልፅነት ችግር አለባቸው እያልን ያለነው የብረታ ብረትና ኢንጂነሪን የሚባለው አስማተኛ ድርጅት የሚሰራው ሰራ የሚያገኘው ገቢና ወጪው በግልፅ አይታወቅም ነው፡፡ እጅግ ብዙ ሀብት ፈሶበትም የሚያመጣው ትርፍ ተመጣጣኝ አይደለም እያልን ነው፡፡ በቅርቡ ከመንግሰት ድርጅቶች ይገዛው የነበረውን የወዳደቁ ብረቶች ግዢ እንዲያቆም መታዘዙ ይታወቃል፡፡ ለምን? የፀረ ሙስና እና ሰነምግባር ኮሚሸን እነዚህ ተቋማት ለምዝበራ የተጋለጡ እንደሆነ ሪፖርት አቅርቧል፡፡ ለነገሩ ይህ ድርጅት ተጠሪነቱም ለመንግሰት የልማት ድርጅት አይደለም፡፡ ሌሎቹም ኮርፖሬሽኖች ለምሳሌ የሰኳር ኮርፖሬሽን ስር ነው የሚባለው ተንዳሆ የሰኳር ፕሮጀክት ያለበትን ጉድ የማያውቅ ያለ አይመስለኝም፡፡
በጀት ውስጥ የገባውን የመከላከያ በጀት ስንመለከት ደግሞ በየሳምንቱ እሁድ በሚያቀርበው የቴሌቪዥን ፕሮግራ በነፃ ገበያ ሰርዓት እየተወዳደረ መነገዱን ቢነግረንም፡፡ በግልፅና በሰውር የሚሰራቸው የገቢ ማስገኛ ገንዘቦች እንዳሉት እየታወቀ ከውስጥ ገቢ የሚባል አንድም የገቢ ርዕስ በጀቱ ላይ አይታይም፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ የመከላከያ በጀት ይህ ብቻ ነው ብሎ ለመውሰድ አይቻልም፡፡ የመንግሰት ጡንቻ በመከላከያ በኩል ከዚህ እንደሚበልጥ ለማወቅ ደግሞ ልዩ እውቀት አይጠይቅም፡፡ ለዚህ ነው የመንግሰትን ትክክለኛ ቁመና የሚያሳይ በጀት አይደለም የምንለው፡፡
እነዚህ እርዳታ እየሰጡን ብድር የማይሰጡን መንግሰታት ምክንያታቸው ምንድነው? ብሎ መጠየቅም ተገቢ ይመሰለኛል፡፡ በኒዮ ሊብራል አሰተሳሰብ ተፈርጀው ሀገራችን ላይ የቀለም አብዮት ሊያመጡ ያሴራሉ የሚባሉት ሀገራት በዋና ዋና የንግድ እና ኢንቨስትምነት ውስጥ እጃቸውን ለማስገባት ወደኋላ ያሉት ለምንድነው? በተቃራኒው ደግሞ ቻይና በእነዚህ ወሳኝ የኤኮኖሚና የንግድ ኢንቨስትመንት ውስጥ እጇን በሰፊው የምትዘረጋው ለምንድነው? ብሎ መጠየቅ እና መልስ መሻት ግድ ይላል፡፡
በእኔ እምነት የምዕራባዊያን መንግሰታት በኢትዮጵያ ውስጥ ባሉ የኢኮኖሚ መስኮች ውስጥ ለመሳተፍ ውሳኔ የሚሰጡት መንግሰታት ሳይሆኑ በየሀገሮቻቸው ያሉት የግል ባለሀብቶች ናቸው፡፡ የመንግሰታት ድርሻ ለባለሀብቶች ትክክለኛ መረጃ እንዲደርሳቸው ማድረግ እና ተገቢውን ከለላ መስጠት ነው፡፡ የግል ባለሀብቶች ደግሞ መረጃ የሚያገኙት ከኢቲቪ አይደለም፡፡ በተለያየ መልኩ በሀገራችን ያለውን ሁኔታ አብጠርጥረው ያውቁታል፡፡ እንደ ምሳሌ በቅርቡ በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች የተከሰተው ዓይነት ብሔርን መሰረት ያደረገ ብጥብጥ ከፍተኛ ትርጉም አለው፡፡ አንድ አንዶች እንደሚያስቡት በአዲስ አበባ እና በዙሪያዋ ያሉ ከተሞች የተቀናጀ ማሰትር ፕላን ዝግጅት ነው ብለው አይወስዱትም፡፡ የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎችና የሰጋት ደረጃ የሚተነትኑ ድርጅቶች የሚያወጧቸው ሪፖርቶች ትርጉማቸው ከፍ ያለ ነው፡፡ በሀገሪቱ ውሰጥ ያለው የዲሞክራሲያዊ ሰርዓት በተለይም በየምርጫ ወቀት የሚፈጠሩ ሰጋቶች፤ መንግሰት የሚያወጣቸው አዋጆች፣ ደንቦች እና መመሪያዎች ተገማችነት፤ በአጠቃላይ ለኢንቨስትመንት ያለው ምቹ ሁኔታ ወሳኝ ግብዓቶች ናቸው፡፡ ዝም ብሎ በኢቲቪ የሚለፈፍ የገፅታ ግንባታ ፕሮፓጋንዳ ተጠቅመው የኢንቨስትምነት ውሳኔ አይሰጡም፡፡
በተቃራኒው የቻይና መንግሰት በከፍተኛ ደረጃ አፍሪካን ለመቆጣጠር ባለው ፍላጎት መነሻ እንዲሁም ውሳኔ የሚሰጡት የግል ባለሀብቶች ሳይሆን የቻይና መንግሰት በመሆኑ ውሳኔዎች በአብዛኛው ኤኮኖሚያዊ አዋጭነት ብቻ ሳይሆኑ የፖለቲካ ጭምር ናቸው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ቻይና በዓለም ላይ ከፍተኛ ብድር ሰጪ ሀገር ነች፡፡ ለአማሪካ ጭምር፡፡ በቻይና የግል ሴክተሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ ኢንቨስት ለማድረግ ገና አልደረሱም፡፡ ቻይና እንደ ሀገር ያላትን ከፍተኛ ቁጠባ በዓለም ላይ ኢንቨስት ለማድረግ እየተጠቀመችበት ነው፡፡ ቻይና በሙሉ በሚባል ደረጃ የምትሰጠንን ብድር የሚጠቀሙበት የቻይና ኩባንያዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ኩባንያዎች ያለውን ስጋት በሚያካክስ ደረጃ ትርፋቸውን በአጭር ጊዜ ለማግኘት ይገባሉ በአሁኑ ሰዓት ቴሌን የወሰዱት ሁለት የቻይና የመንግስ ኩባንያዎች ናቸው፡፡ በተለያየ ስም የሚሰሩ፡፡ ቻይና የምታስገርመው እነዚህ የመንግሰት ኩባንያዎች ጉቦ የመሰጠት ጭምር አቅም አላቸው፡፡
እንደ ማጠቃለያ ለኢትዮጵያ የተበጀተው በጀት ብር 178.6 ቢሊዮን በጀት እንደ ሀገር ሲታይ አጅግ ዝቅተኛ ነው፡፡ ኢትዮጵያ 90 ሚሊዮን ህዝብ የሚኖርባት ከመሆኗ አንፃር እና በቅርቡ ደግሞ ዓመታዊ የነብስ ወከፍ ገቢያችን ብር 11 ሺ (550 የአሜሪካ ዶላር) ደርሶዋል ከተባልን ይህ በጀት ከእያንዳንዱ ሰው በወር የገቢውን 1.5 ከመቶ መዋጮ ሊሸፍነው የሚችለው ነው፡፡
ቸር ይግጠመን