onsdag 10. september 2014

የዘ-ሐበሻ አንባቢያን የዓመቱ ምርጥ ሰው ይፋ ሆነ

ነጻነት፣ ፈጣሪ ለሰው ልጆች ሁሉ በነጻ የሰጠን ገጸ በረከት ነው። ነገር ግን በአገራችን ኢትዮጵያ፣ ጥቂቶች፣ የያዙትን መሳሪያና ያላቸዉን ጡንቻ በመጠቀም፣ ነጻነታችንን ሰርቀዉን፣ በባርነትና በፍርሃት እንድንኖር አድርገዉናል። ከፍርሃት የተነሳ ብዙዎቻችን ከአገር ተሰደናል። ብዙዎቻችን በአገራችን እንደ ሁለተኛና ሶስተኝ ዜጎች ተቆጠረን፣ አንገታችንን ደፍተን፣ በሉ የምናብለውን እያልን፣ ሰልፍ ዉጥ ስንባል ሰልፍ እየወጣን፣ ከፍቃዳችን ዉጭ የጥቂቶችን ፍላጎት ብቻ እየፈጸምን የምንኖር አለን። በፍርሃት ተተብትበንና በጥቅም ታስረን።
person of the year
በሌሎች ትግልና መስዋእትነት ነጻነታችንን ማግኘት የምንፈልግ ጥቂቶች አይደለንም። ነጻነትን ፈልገናት፣ ግን ለነጻነት የሚከፈለዉን ዋጋ ለመከፈል ፍቃደኝነት አይታይብንም። ከታሰርንበት ፍርሃት ለመላቀቅ አልቻልንም።
ነገር ግን ከመቼውም ጊዜ የበለጠ፣ የፍርሃትን ቀንበር በመስበር፣ ለራሳቸው ነጻነትን አዉጀው፣ ለሌሎች መብት የተሰለፉ ብዙ አኩሩ ልጆችን ኢትዮጵያ እያፈራች ነው። እስራትን፣ እንግልትን የማይፈሩ፣ ለአገራቸዉን ለሕዝባቸው መስዋእትነት ለመክፈል የተዘጋጁ፣ ጠመንጃና ጥይት ሳይዙ ጀግንነት ምን ማለት እንደሆነ ያስመሰከሩ ልጆች !
ከነዚህ አኩሪ የኢትዮጵያ ልጆች መካከል፣ በመቀሌ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር የሆነው፣ ታዋቂው ጦማሪ፣ ወጣት አብርሃ ደስታ ይገኝበታል። ወጣት አብርሃ ፣ ከሕወሃት አፍንጫ ሥር ሆኖ ፣ ብዙዎች ያላወቁትንና ያላዩትን፣ በትግራይ ባሉ ኢትዮጵያዊያን ወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ያለዉን ግፍና ጭቆና ሲታግልና ሲያጋልጥ የነበረ ወጣት ነው። ብዙ ጊዜ በሕወሃት ካድሬዎች ተደብድቧል። ተሰድቧል። ዛቻና ማስፈራራት ደርሶበታል። ነገር ግን አብርሃ አልተበገረም። አንዳንዶች እንደሚያደርጉት፣ የሕወሃት አባልና ካድሬ ሆኖ በግሉ የተለየ ጥቅም ሊያገኝ ይችል ነበር። በጥቅም ሊደልሉት ሞክረዋል። ነገር ግን ራስ ወዳድ አልሆነም። ከግል ጥቅም ይልቅ የአገርን እና የሕዝብን ጥቅም አስቀደመ። የህዝቡን ብሶት እያነሳ ጮኸ።
አገራችን ኢትዮጵያን ትልቅ ስጋት ላይ ከጣሉት ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል አንዱ፣ በሕወሃት/ኢሕአዴግ የተዘረጋው የዘር ፖለቲካ ነው። አገዛዙ ትግሬ፣ ኦሮሞ፣ አማራ … እያለ ዜጎችን በመከፋፈል ፣ አንዱን ከአንዱ ጋር በማጣላት፣ ለብዙ ወገኖች እልቂትና መፍናቀል ምክንያት ሆኗል። አብርሃ ደስታ « ብሄሬ(ዘሬ) ኢትዮጵያዊነት ነው» በሚል ዜጎችን በዘራቸው ሳይሆን በስራቸው ብቻ መመዘን እንዳለባቸው የሰበከ፣ በነአጼ ዮሐንስ እና ራስ አሉላ አባ ነጋ መንፈስ፣ የኢትዮጵያዊነትን ደውል ያቃጨለ ብርቅዬ የኢትዮጵያ ልጅ ነው።
ሐሳብ፣ ጽሁፍን መመከት የማይችሉ፣ የጫካ ፖለቲካ የሚያራምዱ ሕወሃቶች ግን ፣ ትችቶችን ተቀብለው ማሻሻያዎችን ከማድረግና የሕዝብ ጥያቄ ከማዳመጥ ይልቅ፣ እንደለመዱት የሚቃወሟቸውን መጨፍለቅ መረጡ። ሐምሌ አንድ ቀን 2006፣ አብርሃ ደሳታን እየደበደቡ አሰሩት። ከመቀሌ ወደ አዲስ አበባ ማእከላዊ ወሰዱት። በሽብርተኝነት ክስ ከሰሱት። ፖሊስ «መረጃ እስካሰባሰብ» ብሎ የ28 ቀን ቀጠሮ ጠየቀ። «ፍርድ ቤቱ» ግን መረጃ ሳያይ፣ የፖሊስን ጥያቄ ተቀበሎ፣ የአብርሃን የዋስታና መብት ረግጦ፣ ለነሐሴ 29 ቀጠሮ ሰጠ። በቀጠሮ ቀን፣ አሁንም ፖሊስ ማስረጃ ያቀርባል ተብሎ ሲጠብቅ እንደገና ተጨማሪ 28 ቀን መረጃ ለማሰባሰ ጠየቀ። ፍርድ ቤቱ እንደገና ሁለተኛ ቀጠሮ ለመስከረም 22 ሰጠ። አብርሃ ደሳታ፣ ምንም አይነት መረጃ ባልቀረበበት ሁኔታ ይኸው ፣ በማእከላዊ እሥር ቤት እየማቀቀ ይገኛል።
አብርሃ ደስታ ሊታሰር እንደሚችል ያውቅ ነበር። ነገር ግን የዜጎችን የነጻነት ጥያቄ፣ ጥቂቶች አፍነው ማቆየት እንደማይችሉ በመረዳቱና፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች፣ ምሳሌ አግኝተው፣ ይበረታቱ የዘንድ፣ የትግል ቁርጠኝነትን ያሳየው።
የኢትዮጵያን ትንሳኤ ለማየት፣ እንደ አብርሃ ደስታ ያሉ በየክልሉና በየቦታው በብዛት መነሳታቸው አስፈላጊ መሆኑን በመረዳት፣ ኢትዮጵያዉያን ሁሉ በያለንብት የአብርሃ ደስታን ፈለግ ተከትለን፣ ለሕግ የበላይነት ፣ ለሰብአዊ መብት መከበር፣ ለነጻነት፣ ለኢትዮጵያነት እንቆም ዘንድ ጥሪ እናቀርባለን። ላባረከተው ትልቅ አስተዋጾ፣ ላሳየው ቁርጠኝነት፣ ከአንባቢያኖቻችንም ብዙ ባገኘው ብዙ ድምጽ መሰረት፣ አብርሃ ደስታን የ2007 የዘ-ሐበሻ አንባቢያን የዓመቱ ሰው መሆኑን ስናሳወቅ በታላቅ አክብሮት ነው።
በአገር ዉስጥና ከአገር ዉጭ የምንኖር ኢትዮጵያዉያን ሁሉ መልካን እንቁጣጣሽ እየተመኘን ፣ 2007 የለወጥ፣ የሰላም፣ የነጻነት አመት እንዲሆንልን ምኞታችንን እንገልጻለን።

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar